አለማየሁ እሸቴ

3 መስከረም 2021

የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሙዚቃ ሲነሳ በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱ ድምጻውያን መካከል አንዱ ነው። ከኢትዮጵያ ዘመናዊ የሙዚቃ ሸክላ ህትመትም ጋር ስሙ አብሮ ይነሳል።

alemayehu eshete
አለማየሁ እሸቴ

የሙዚቃ ሥራቸውን በሸክላ ቀድመው ካሳተሙ የመጀመሪያዎቹ ድምጻዊያን መካከል አንዱ እንደሆነ ይነገራል-አንጋፋው ድምጻዊ አለማየሁ እሸቴ።

አለማየሁ የተለያዩ ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎቹ በሙዚቃ ወዳጆች ልብ ውስጥ ከፍ ያለ ክብር አስገኝተውለታል።

በቄንጠኛ አለባበሱና የፀጉር ስታይሉ [አበጣጠሩ] በዘመኑ ወጣቶች ልብ ውስጥ የገባም ነበር።

ድምጻዊ አለማየሁ ነሐሴ 27 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረበት የልብ ህመም ምክንያት በ79 ዓመቱ በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል።

ድምጻዊ አለማየሁ የተወለደው በአዲስ አበባ ከተማ ሲሆን እስከ ሦስት ዓመቱ ድረስ ከእናቱ ጋር ደሴ ነበር ያደገው። ከዚያም የሦስት ዓመት ልጅ ሳለ አባቱ ወደ አዲስ አበባ አመጡት።

አዲስ አበባ መጥቶም ‘ክርስቲያን ትሬኒንግ ኢንስቲቲዩት’ አዳሪ ትምህርት ቤት ገብቶ ትምህርቱን መከታተሉን ለሸገር ተናግሮ ነበር።

በትምህርት ቤቱም መንፈሳዊ መዝሙሮችን በመዘመር ይታወቅ ነበር፤ በእንግሊዝኛ ቋንቋም ጭምር። ድምጹም እጅግ የተወደደ ነበር።

እንዲህ እንዲህ እያለ የሙዚቃው ስሜት እየኮረኮረው መጣ። በዘመኑ ተወዳጅና እውቅ የነበሩ የምዕራባውያን ድምጻውያንን ሙዚቃ ማንጎራጎር ያዘ።

በተለይ የሮክ የሙዚቃ ስልት ለአለማየሁ ነፍሱ ነበር።

የአሜሪካውያኑን ድምጻዊያን ፓት ቦን፣ ቢል ሃሊይ እና ኤልቪስ ፕሪስሊን የእንግሊዝኛ ዘፈኖች አብዝቶ ይጫወት ነበር።

የኤልቪስ ፕሪስሊን ሙዚቃ አብዝቶ በመጫወቱ፣ በፀጉር አበጣጠሩና ዘመናዊ አለባበሱ ‘ኢትዮጵያዊው ኤልቪስ’ የሚል ቅፅል ስምም ተሰጥቶታል።

አለማየሁ ስለፀጉር አበጣጠሩ “የፀጉር ስታይሉ ረዥም ስለነበር፤ ፀጉሬ አፍንጫየን ሸፍኖት ነበር የምሄደው” ሲል በአንድ ወቅት ለሸገር ራዲዮ በሰጠው ቃለ ምልልስ ላይ ተናግሮ ነበር።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጀግናው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ገድል!! - ይድነቃቸው ከበደ

በዚህ እውቅናን እያተረፈ የመጣው አለማየሁ በጀነራል ዊንጌት፣ በዳግማዊ ምንሊክና በሌሎችም ትምህርት ቤቶች እየተጋበዘ ይዘፍን ነበር።

በወቅቱ ለአማርኛ ዘፈን ግድ አልነበረውም፤ እምብዛም አይጫወትምም ነበር።

አለማየሁ እሸቴ

“ከዘፈንኩም የጥላሁን ገሠሠን ‘እንክርዳድ እንክርድድ የተንከረደደ’ የሚለውን ነበር” ብሏል በዚያው ለሸገር በሰጠው ቃለ ምልልስ ላይ።

ለዚህ ደግሞ ይመለከታቸው የነበሩ የምዕራባውያን ፊልሞች አስተዋፅኦ ነበራቸው።

በአዲስ አበባ እምብርት -ፒያሳ የነበረው ‘አድዋ ሲኒማ’ እና አሁንም ድረስ ያሉት ‘ኢምፓየር’ እና ‘ኢትዮጵያ’ ሲኒማ ቤቶች በወቅቱ የሚያሳዩት የምዕራባውያን ፊልሞችን ነበር።

አለማየሁ ጎራ እያለ የሚኮመኩማቸው እነዚህ ፊልሞች የልጅነት ቀልቡን ይስቡት ነበር።

በሆሊውድ የፊልምና የሙዚቃ ሥራ ልቡ የሸፈተው አለማየሁ ወደዚያው ሊያቀናም ጉዞ ጀምሮ ያውቃል።

አለማየሁ ከአባቱ ኪስ ያገኛትን መቶ ብር ይዞ ነበር ከጓደኛው ጋር ሆሊውድ ለመድረስ መንገድ የጀመሩት፤ ይሁን እንጂ ያለሙበት ሳይደርሱ ምጽዋ ላይ ተይዞ ወደ ቤተሰቡ ተመልሷል።

እዚያ በቆዩበት ጊዜም ያቀነቅናቸው በነበረው ምዕራባውያን ዘፈኖቹ የምፅዋ መርከበኞችን በፍቅሩ ጥሏቸው እንደነበር ይነገራል።

አለማየሁና የሙዚቃ ሥራዎቹ

ድምጻዊ አለማየሁ እሸቴ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አዲስ አበባ ውስጥ በአርበኞች ትምህርት ቤት እየተከታተለ ባለበት ወቅት ነበር ነፍሱ ለሙዚቃ አድራ በ1955 ዓ.ም የፖሊስ ሠራዊት ኦርኬስትራን የተቀላቀለው።

እዚያው ፖሊስ ኦርኬስትራ ውስጥ እስከ 1961 ዓ.ም ድረስ የሙዚቃ ሥራዎቹን ለአድናቂዎቹ አድርሷል።

ከዚያ በኋላ በሮሃ ባንድ፣ በሸበሌ ባንድ፣ በአይቤክስ ባንድ፣ በዓለም ግርማ ባንድ፣ የራሱ በሆነው ሶሊኮስ ባንድ እና በሙላቱ አስታጥቄ ባንድ በርካታ የሙዚቃ ሥራዎችን አበርክቷል።

‘የወይን ሐረጊቱ’፣ ‘እንዲህ ነው ወይ መውደድ’፣ ‘ማሪኝ ብየሻለሁ’፣ ‘ማን ይሆን ትልቅ ሰው’፣ ‘እንደ አሞራ’፣ ‘ምሽቱ ደመቀ’፣ ‘ችግርሽ በእኔ አልፏል’፣ ‘የሰው ቤት የሰው ነው’፣ ‘ደንየው ደነባ’፣ ‘ወልደሽ ተኪ እናቴ’፣ ‘ለሰሚው ይገርማል’፣ ‘ማን ይሆን ትልቅ ሰው’፣ ‘ስቀሽ አታስቂኝ’፣ ‘የአባይ ዳር እንኮይ’፣ ‘ኮቱማ ፍቅርዬ’፣ ‘አዲስ አበባ ቤቴ’፣ ‘እንግዳዬ ነሽ’፣ ‘ተማር ልጄ’ እና ሌሎችም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዓለማየሁ ገላጋይ

‘ተማር ልጄ’ እስካሁንም ድረስ ወላጆች ልጆቻቸውን የሚገስፁበትና የሚመክሩበት እንዲሁም የትምህርት ጉዳይ በሚወራበት ቦታ ሁሉ የሚነሳ የሙዚቃ ሥራው ነው።

ይህ የሙዚቃ ሥራው ከተሠራ ከ35 ዓመታት በላይ አስቆጥሯል። በዚሁ ዘፈኑም እአአ በ2015 በጀርመን አገር ሽልማት ተበርክቶለታል።

ድምጻዊው በሥራዎቹ በኢትዮጵያ በሚዘጋጀው የ5ኛው ለዛ ሽልማት የሕይወት ዘመን ተሸላሚም ነበር።

“በብዙኃኑ ሀቅ የሚሸቅጥ አርቲስት መሆን አይገባውም”

አለማየሁ ኪነ-ጥበብ የዘመኑን ሀቅ ይዞ መሄድ አለበት የሚል እምነት አለው። ለዚህም ነው ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸው ዘፈኖችን ያለ ፍርሃት ያቀነቀነው።

“ሃይ ዘራፍ እያሉ እያረረ አንጀቴ፣

እኔስ አረባሁም ወልደሽ ተኪ እናቴ” የሚለውን የፍትሕና እኩልነት መጓደልን የተናገረበትን ስንኝ በዋቢነት መምዘዝ ይቻላል።

“በሕይወቴ መፍራት አልወድም። አርቲስት ማለት ብዙኃኑ ሲራብ የሚራብ፣ ሲቸገር የሚቸገር፣ ታሪኩንና ጀግንነቱን በግልጽ የሚናገር እንጂ የብዙኃኑን ሀቅ የሚሸቅጥ ከሆነ አርቲስት መሆን አይገባውም” ሲልም በአንድ ወቅት ተናግሮ ነበር።

ድምጻዊ አለማየሁ እሸቴ በቤተሰብ ሕይወቱም በአርአያነት ይጠቀሳል። የዝነኛነትን ጎራ ሳይቀላቀል ከተዋወቃት ፍቅረኛውና ባለቤቱ ጋር ከአርባ ዓመታት በላይ በሞቀ ትዳር ውስጥ ቆይቷል። ሰባት ልጆችን አፍርተው የልጅ ልጅም አይተዋል።

አለማየሁ ባለቤቱን ‘አባየ’ ሲል ነው የሚጠራት። በአንድ ወቅት ምክንያቱን ተጠይቆ “እናቴ ከሞተች በኋላ እናቴ እርሷ ናት” ሲል ነበር የመለሰው። ‘በአገርና በሚስት ቀልድ የለም’ ከሚሉት ወገንም ነበር አለማየሁ።

የአለማየሁ እሸቴ ድንገተኛ ህልፈት በርካቶችን አስደንግጧል፤ በርካቶችም የተሰማቸውን ሐዘን እየገለጹ ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published.