የጀግናው ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ገድል!! – ይድነቃቸው ከበደ

+ይህ ብርቅዬ ጀግናችን እስካሁን በሕይወት ይኑር አይኑር በይፋ የታወቀ ወይም የተነገረ ነገር የለም ፤እንዲያም ተባለ እንዲህ ጀግናችን በልባችን ውስጥ ህያው ሆኖ ይኖራል !!! ]

ለሀገራችን ሉዓላዊነት ለማስከበር በግንባር ቀደምትነት ተሰልፈው ታላቅ ገድል ከፈፀሙ በርካታ ጀግኖች መሀል አንዱ ነው፡፡ በፈፀመው ወደር የሌለው ጀግንነት ሊታወስ የሚገባ የሀገር ኩራት። ነገር ግን ጀግንነቱ በወጉ ያልተነገረለት፡፡

ጀግናው ለኢትዮጵያ አየር ኃይል ዘላለማዊ ኩራት ከሆኑ ድንቅና ብርቅዬ ተዋጊዎች መሃል በጀግንነቱ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ ነው፡ ፡

በ1944 ዓም የተወለደው ይህ ብርቅዬ ጀግና ታላቅ ገድል ከፈፀመባቸው የውጊያ ውሎዎቹ መሃል የሐምሌ 27 ቀን 1969 ዓ.ምህረቱ ይቀድማል፡፡ በዚያ ወቅት ትምክህተኛው የዚያድ ባሬ መንግስት በምስራቅ ኢትዮጵያ ግዙፍ ወታደራዊ ወረራ ይፈፅሞ ነበር፡፡ ይህንን ወረራ ለመመከት ከተሰማሩት የአየር ኃይል (አሜሪካ ሰራሽ ኤፍ 5 ኢ) ተዋጊ ጀቶች መሃል አንዱን የያዘው ይህ ጀግና ነበር።

እናም በኦጋዴን ሐረዋ፣ አይሻ፣ በእነኖ ሜጢ እና በሌሎችም ቦታዎች የሮኬት ናዳ በማውረድ ወራሪውን የሶማሊያ ጦር ባለበት እንዲገታ ከማድረግ ባሻገር፣ 8 የጠላት ታንኮችን ከእነምድብተኛው ረመረመ፡፡ ይህንን ታላቅ ጀግንነት ባስመዘገበ በ10 ሰዓት ልዩነት እንደገና ወደ ምስራቅ ጦር ግንባር በመብረር የኢትዮጵያን አየር ኃይል ብቃት ያስመሰከረም ነው፡-

ይህ ጀግና።ገድሉ ይቀጥላል፡-…..

ጥቅምት 7 ቀን 1970 ዓም፡፡ የኢትዮጵያ ሠራዊት በጅጅጋ ካራማራ ላይ ከፍተኛ ትንቅንቅ ላይ ይገኛል፡፡ ያኔ እሱ ከላይ ከሰማይ በሚያወረደው ቦንብ የሶማሊያን ወራሪ ጦር ብትንትኑን ማውጣት ተያያዘ፡፡ በዚህ ጊዜ ከጠላት ወገን በተተኮሰ አየር ቃወሚያ የሚያበረው ኤፍ 5 ኢ ተዋጊጀት ተመታ፡፡ ይኼኔ እሱ በዥንጥላ ወርዶ ህይወቱን ማትረፍ ነበረበት፡፡ ነገርግን የሚያበረውንም ጀት ጭምር እንጂ የራሱን ህይወት ብቻ ማትረፍ አልፈቀደም፡፡ እናም የሚያበረውን ጀት በቆራጥነት እየቀዘፈ ወደ ቢሾፍቱ አየር ማረፊያ ገስግሶ በሰላም አረፈ፡፡ የተመታውም ጀት ተጠግኖ እንደገና ለግዳጅ ተሰማራ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሊቀ ሊቃውንት ጌታቸው ኀይሌ (1931-2021)

ሐምሌ 30 ቀን 1969 ዓ.ም በነገሌ ቦረና ግንባር የተሰማራውን የሶማሊያ ጦር የቦንብ ናዳ በማውረድ ጠላትን ብትንትኑን ማውጣቱን ቀጠለ፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፤ሁለት የሶማሊያ ጦር ጀቶችን በአየር ላይ አጋይቶ ጣለ፡፡ የሚገርመው አንዱን የሶማሊያ ጦር ጀት ያጋየው ሶማሊያ ግዛት ውስጥ ዘልቆ ገብቶ መሆኑ ነው፡፡

አሁንም የጀግናው ገድል ይቀጥላል፡-

.

ጥቅምት ወር 1970 ዓ.ም፡- የሶማሊያ ጦር ጀቶች ድሬደዋ ከተማ ላይ ጥቃት ፈፀሙ፡፡ ይኼኔ ለጥቃቱ የአፀፋ መልስ እንዲሰጡ የኢትዮጵያ አየር ኃይል ተዋጊዎች ታዘዙ፡፡ ከታዘዙት ተዋጊዎች መሃል አንዱ ይህ ጀግና ነበር፡፡እናም ጀቱን እየቀዘፈ የአየር ላይ ትርዒት ጭምር በማሳየት ጀግናው ገድሉን ቀጠለ፡፡ እናም የሶማሊያን ሚግ 21ተዋጊ ጀት ከነአብራሪው በአየርላይ አጋይቶ በሰላም ወደ ቢሾፍቱ ተመለሰ፡፡ እነሆ ይህ ጀግና እንዲህ ያለ አኩሪ ገድል የፈፀመ ነው፡፡

ማነው?

ይህ ጀግና ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ይባላል፡፡ (በነገራችን ላይ ኮሎኔል በዛብህ፤የፕር በየነ ጴጥሮስ ወንድም ነው፡፡) ከላይ የጠቀስነውን ጀግንነት በፈፀመ ጊዜ የሻለቅነት ወታደራዊ ማዕረግ ነው የነበረው፡፡ የሆነ ሆኖ የጀግናችንን አኩሪገድል መተረካችንን እንቀጥል፡፡

ሕዳር 3 ቀን 1970 ዓ.ም፡፡የሶማሊያ ተዋጊ አውሮፕላኖች ወደ ኢትዮጵያ ገብተው ጥቃት ፈፅመው ተመለሱ፡፡ ይኼኔ ሁለት የኢትዮጵያ ተዋጊዎች (ሻለቃ በዛብህ ጴጥሮስ እና ኮሎኔል ለገሰ ተፈራ) ተከትለዋቸው ገሰገሱ፡- እስከ ሞቃዲሾ ድረስ፡፡ የሶማሊያ አውሮፕላኖች ሞቃድሾ አየር ማረፊያ ደርሰው ለማረፍ ዝቅ ሲሉ፤ ጀግኖቹ ሻለቃ በዛብህና ኮሎኔል ለገሰ ተፈራ እዚያው ደፍቀው አጋዩአቸው፡፡ እናም በሰላም (እየሸለሉ) ወደ ቢሾፍቱ ተመለሱ፡፡ ይህ የጀግኖቻችን ተግባር ለሶማሊያውያን ዘላለማዊ ውርደት ያከናነነበ እንደ ነበር ታሪክ ይመሰክራል፡፡

የጀግናው በዛብህ ጴጥሮስ ገድል ይቀጥላል፡-

ታህሳስ 13 ቀን 1970 ዓም በዛብህ፤ ቶጎ ውጫሌ በሚባል ቦታ ላይ የሚገኝን የሶማሊያ ጦር መሳሪያ ግምጃ ቤት እና መካናይዝድ ክፍለ ጦር መምሪያ በቦንብ እያጋየ ሳለ ከጠላት ወገን በተተኮሰበት አየር መቃወሚያ ጥይት የሚያበረው አውሮፕላን ሞተር ክፍል ተመታበት፡፡በዛብህ ጴጥሮስ አውሮፕላኑ ክፉኛ ቢመታም አልተደናገጠም፡፡ የተመታውን አውሮፕላን መልሶ ደብረዘይት ለማሳረፍ ታላቅ ጥረት አደረገ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለጀግናው ኮ/ል በዛብህ ጴጥሮስ የመታሰቢያ ሐውልት ቆመ (ጌጡ ተመስገን)

ሆኖም ጥረቱ አልተሳካም የአውሮፕላኑ ነዳጅ አለቀበት፡፡ በዚህ የተነሳ ቢሾፍቱ እና ሞጆ መሃል በሚገኝ ገላጣ ሜዳ ላይ አውሮፕላኑን አሳርፎ ድርብ ጀግንነቱን አስመሰከረ፡፡ጀግናው በዛብህ ጴጥሮስ፤ በኢትዮጵያና በሶማሊያ ድንበር ተፈሪ በር በተባለ የጦር መንደር ላይ የሚገኘውን (በጥር ወር 1970) የከባድ መሳራያ ግምጃ ቤት እና የጠላት ጦርም ድባቅ መታ፡፡ በዚህ ወቅት 5 የጠላት ታንኮችን ከነምድብተኛቸው ደመሰሰ፡፡

ይሁን እንጂ አሁንም ከጠላት በተተኮሰ ፀረ አውሮፕላን ጥይት ተመቶ የሚያበረው አውሮፕላን በእሳት ተያያዘ፡፡ ጀግናው ይህም ጥቃት አላሸበረውም፡፡ እሳቱን በመከላከያ በማጥፋት ወደመጣበት ተመለሰ፡፡ አሁን ግን ቢሾፍተቱ መድረስ አልቻለም፡፡

አውሮፕላኑን ድሬደዋ አየርማረፊያ አሳረፈው፡፡አውሮፕላኑም ተጠግኖ እንደገና ለግዳጅ በቃ፡፡ይህ ጀግና ፤ ከሚያዝያ ወር 1970 ጀምሮ ኤርትራ ወደ ሚገኘው 2ኛው አየር ምድብ እንዲዛወር ተደረገ፡፡ ሻለቃ በዛብህ ጴጥሮስ የሶማሊያን ወረራ ለመቀልበስ ከሐምሌ ወር 1969 እስከ የካቲት ወር 1970 በተደረገ የመከላከልም ሆነ የማጥቃት ውጊያ 191 ጊዜ ወደ ጠላት ወረዳ በርሯል፡፡

በዚህ የላቀ እና ታላቅ ሀገራዊ ተጋድሎ ላበረከተው አስተዋፅኦ በወቅቱ የነበረው የኢትዮጵያ መንግስት

መስከረም 3 ቀን 1972 ዓ.ም “የላቀ የጦር ሜዳ ጀብዱ ሜዳይ” ሸልሞታል፡፡

.

እዚህ ላይ ሻለቃ በዛብህ ጴጥሮስ ህዳር 21 ቀን 1972 ዓም ለንባብ በበቃው “ታጠቅ” የተሰኘ የሰራዊቱ ጋዜጣ ላይ ከሰጠው ቃለምልልስ የሚከተለውን መጥቀስ ይገባል፡፡ እነሆ፡-

“… እኛ ብንሞት ሌላ ሰው ይተካናል፤ መተኪያ የሌላት ሀገር ከሞተች ግን ተተኪው ትውልድ ስለሚሞት ዋጋ አይኖረውም ፡፡ የሀገርን ሉአላዊነት በአስተማማኝነት መጠበቅ ቆራጥነት እና ልበ ሙሉነት ይጠይቃል፡፡ እኛ በሕይወት ቆመን እያየን ጠላት አንዲት ስንዝር መሬት ቆርሶ መሄድ ቀርቶ በአንድ እግሩ እንኳ ሊቆምባት አይችልም፡፡ ከሀገር ወዲያ ሌላ መኖሪያ ዋሻ ስለሌለ በሃገርና በነፃነት ጉዳይ ምንም ቀልድ ሊኖር አይችልም፡፡…”

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ማነዉ? ክፍል አንድ (በንጉሤ ዶሌቦ)

.

ይህ ጀግናችን የተናገረውን ካለማወላወል በተግባር የፈፀመ ብርቅዬ ልጅ ነው፡፡ ከሶማሊያ ወረራ በኋላ ወደ ኤርትራ ዘምቶ እስከ 1977 ድረስ ግዳጁን በአግባቡ የተወጣ አርበኛ ነው፡፡ በ1977 ዓም ግን ከሻዕቢያ ጋር በናቅፋ ግንባር እየተዋጋ ሳለ አውሮፕላኑ ተመታ፡፡ አሁን ግን ወደ ተነሳበት ቦታ መመለስ አልቻለም፤በሻዕቢያ እጅ ወደቀ ጀግናችን እስረኛ ሆነ፡፡

በ1983 ዓም ከእስር ተለቆ ከቤተሰቡ ጋር መቀላቀልም ችሎ ነበር፡፡ከሰባት ዓመት በኋላ በ1990 ዓም የኢህአዴግ ወዳጅ የነበረው ሻዕቢያ ጠላት ሆኖ መጣ ተባለ፡፡ ባድመን ወረረም ተባለ የሦሥት ወንዶች እና የሁለት ሴቶች አባት የሆነው ኮሎኔል በዛብህ የሀገሩን ክብር ለማስመለስ እና ሻዕቢያን ለመደምሰስ ዳግም ዘመተ፡፡

እንደ ልማዱ ተዋጊ አውሮፕላኑን እየሰገረ የሻዕቢያን ጦር አከርካሪ መሰባበሩን ቀጠለ፡፡ግንቦት 5 ቀን 1990 ዓም ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ወደ ኤርትራ ምድር ዘልቀው ከገቡ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ተዋጊዎች አንዱነበር፡፡ የሚያበረውን አውሮፕላን ዝቅ፤….እጅግ ዝቅ….. አድርጎ የሻዕቢያን ጦር “አፈር ድሜ እያስጋጠ “ ሳለ ተመታ፤ እንደገና በሻዕቢያ እጅ ወደቀ፡፡ የሻዕቢያ እስረኛ ሆነ፡፡

እነሆ ይህ የሀገር ፈርጥ፤ ይህ ብርቅዬ ጀግናችን እስካሁን በሕይወት ይኑር አይኑር በይፋ የታወቀ ወይም የተነገረ ነገር የለም፡፡ “አውራምባታይምስ” ድረ ገፅ ኦክቶበር 16፤2013 ከሕውሐት መሪ ስብሃት ነጋ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ ጀግናችን ሳይገደል እንዳልቀረ ጠቁሟል፡፡

ያሳዝናል፡፡ እንዲያም ተባለ እንዲህ ጀግናችን በልባችን ውስጥ ህያው ሆኖ ይኖራል፡፡ እኛ ገድሉን እንዘክራለን፡፡ በታሪካችን ውስጥ ከፍ ከፍ እያደረግን እናወሳዋለን፡፡ የኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ታሪክ እና ገድል ከመቃብር በላይ ነውና….

2 Comments

  1. እናመሰግናለን እኛም ቀደም ባለው ጊዜ እሱንና ኮለኔል ታደሰንና ሌሎች ወገኖቻችንን እንዲፈቱልን አስመራ ውርውር የሚሉትን ጩሉሌ የግንቦት ፯ ድርጅት መሪዎችን ጠይቀን ነበር። ባረመኔው ኢሳይያስ አፈወርቅ ሞገስ ለማግኘት እንደውም ወንጀሉን ለማብዛት ዴዳቸው። ወንድሙ ያልከውም ከአሳሳሪዎቹ ህወአት ጋር ሲሞዳሞድና ለቁሳዊ ፍላጎቱ ከመጋጋጥ ያለፈ ያደረገውን ጥረት አላየንም።

    ኮለኔል በዛብህ በህይወት እንዳለም ይነገራል ኮለኔል በዛብህ የደቡብ ሰው ነው አብይ መሀመድ አሳሪውን ኢሳይያስ አፈወርቅን ለጉብኝት የወሰደው አዋሳ ነው ተጎብኝውም ህዝብ ውድ ልጁን ላሰረበት አረመኔ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ወጥቶ በዛ ክብር መቀበሉ በዛብህ ጴጥሮስ በህይወት ቢኖርም ግደለው ከማለት የተናነሰ አይደለም።

    ለማንኛውም የዚህ ጀግና ገድል በሚገባ አልተዘከረም ወደፊት ኢትዮጵያዊ ትውልድ ሲበዛ ታሪክ ትክክለኛ ክብሩን ትሰጠዋለች ብለን እናምናለን።

Leave a Reply

Your email address will not be published.