ዜጎች ከፍትህ ምንጭ ጠጥተው ይረኩ ዘንድ – ገለታው ዘለቀ

286343088 564576025196718 8022583426552624767 nሃገራችን ኢትዮጵያ በከፋ ስርአታዊ ሽብር ላይ እስከ አሁን ድረስ እንዳለች አለች። ፍርድ ቤት በዋስ የለቀቀውን ፓሊስ ለፍርድ ቤት አልታዘዝም ብሎ ትእዛዙን ሲንቅና በተቋማት መካከል ግጭት ሲፈጠር፣ በክልሎች መካከል ግጭትና አለመተማመን ዳብሮ ሁሉም በየራሱ ወታደር ሲያሰለጥን፣ የውስጥ መፈናቀል (IDP) በሃይል ሃገሪቱን ሲያምስና የማያባራ ክስተት ሲሆን፣ በመንግስት ባለስልጣናት መካከል የቋንቋ መደበላለቅ ሲኖር፣ የመተማመን መትነን (trust evaporation) በሃይል ሲታይ፣ የእርስ በርስ ግጭትና ጦርነት ሲበዛ……….. የለሂቅ ክፍፍል ሲጨምር…… ያ…. ሃገር ስርአታዊና መዋቅራዊ ሽብር (structural and systemic violence) ላይ እንደተጣደ ምልክት ይሆናል። ይህ ችግር ሲከሰት  ፈጠን ብሎ ሃገሪቱ የተውጣጣ የሽግግር መንግስት መስርታ በረጋ መንፈስ የስርዓትና የመዋቅር ለውጥ እንድታመጣ መስራት ያስፈልጋል። ችግሩ መዋቅራዊና ስርዓታዊ ሆኖ እያለ በዚህ ዙሪያ ለውጥ በዘገየ ቁጥር ክፉ ነገሮች ሁሉ እየፋፉ እየፋፉ ይመጡና ሃገር ያወድማሉ።

ግጭትና መፈናቀል አምራች በሆነ መዋቅርና ስርዐት ስር በዋልን ባደርን ቁጥር ፍትህና ፀጥታ ከሃገራዊ ጠገጋችን ስር ይተንናሉ። ፍትህ ሲጠፋ የነፍስ ፅዳት በማህበራችን ውስጥ አይኖርም። የህብረታችን ህሊና ይቆሽሻል። ፍትህ የህብረታችን ህይወት ማሳለጫ የመንገዳችን ርቱእነት መለኪያና ማረጋገጫ  ነው።

ፍትህ  ከተበላሸ ስርዓት አይቀዳም። በውኑ ከመራራ ምንጭ ጣፋጭ ውሃ መጠጣትና መርካት እንችላለን? አይቻልም። ፍትህም እንደዚህ ነው። ሃገራችን የፍትህ ስርዐቷን ስታዋቅር የፍትህ ተቋሞቿን ሁሉ  የብሄር ስም ሸልማለች፣ የኦሮሞ ፓሊስ፣ የትግሬ ፓሊስ ፣ የጉራጌ ፍርድ ቤት የአማራ ፍርድ ቤት ወዘተ ብለን ለኢትዮጵያዊያን ሁሉ  ከፍትህ ማእድ እንጀራ እንዲቆርሱ ከዚህ ምንጭ ጠጥተው እንዲረኩ ማድረግ ከቶውንም አይቻልም። የብሄር ጥብቆ የለበሱ ፓሊሶችና ዳኞች እነሆ ከፍትህ ማእድ ላይ አሳላፊም አስተናጋጅም አይሆኑም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በመርካቶ የ32 ቀበሌ ወጣቶች በብዛት ታሰሩ፣ ሰፈራቸውን ለቀው እየጠፉ ናቸው

በአለም ታሪክ ውስጥ አንድ ጊዜ ፍትህ የሚባለውን ረቂቅ ሃሳብ ሰአሊዎች እንዲስሉትና ይህ ስእል የፍትህ ሃውልት እንዲሆን ተጠይቆ ነበር። ፍትህን በምልአት የሚገልፅ ስዓሊ ባይገኝም ነገር ግን አንዲት ሴት ሚዛን ይዛ በህሊናዋ ሚዛኑ እኩል ሆኖ እያየች ነገር ግን እነዚያ ስጋዊ አይኖቿ ግን በጨርቅ ታስረው የሚያሳየው ስእል ተመራጭ ሆኖ እነሆ ዛሬ በአለም ላይ የፍትህ ምልክት ሆኖ ሃውልት ተሰርቶለት ከብዙ ፍርድ ቤቶች ግቢ ቆሞ ይታያል። ኢትዮጵያ ውስጥ ልደታ ፍርድ ቤት ግቢ ውስጥ ይህንን ሃውልት አይቻለሁ። ነገር ግን የሃገራችን የፍትህ ተቋማት ለብሄርተኝነት አይናቸው የተገለጠ በመሆኑ በገሃድ የብሄር ፍርድ ቤት ነኝ ብለው የቆሙ ፍርድ ቤቶች ባሉበት ሃገር ዜጎች ከፍትህ እንጀራ አይጠግቡም። የኢኮኖሚ ፍትህ፣ ማህበራዊ ፍትህ፣ የፓለቲካ ፍትህ ሁሉ ስጋዊ አይናቸው ባልታሰረ ሰዎች ከቶውንም እውን አይሆኑም። የማንነት ፓለቲካ ትልቅ ችግር ሲስተሚክ ቫዮለንስን የሚወልድ በመሆኑ ስጋዊ አይን ( blood line eyes) ቦግ አድርጎ ከፍቶ ፍትህን ይረመርማል።

ፍትህ በሃገሪቱ ሰማይ ስር ሲረብብ ምቾት ህዝቡን ስለሚሰማው ነጋዴው ተግቶ ይሰራል፣ ባለሙያው ፈጠራው ይጨምራል….። ፍትህን የተረዱ መሪዎች የሚያስፈልጉን ለዚህ ነው። የመንግስት ዋና ስራ ንግድ  ውስጥ ገብቶ መከሰብ ሳይሆን ለፍትህ ማደግ አሜኬላ የሆኑ ስርዓቶችን እየነቀሱ በማውጣት ለፍትህ እርሻን ማለስለስ ነው። ይህንን ማድረግ ሲቻል ህብረታችን እየተሳለጠ ይሄዳል። እውነት ነው የሰው  ልጅ ፍጹም ባለመሆኑ አንዳንድ ችግሮች በማህበሩ ውስጥ ሁሌም ይከሰታሉ ነገር ግን ማይክሮ ግጭቶች ወደ ማክሮ ደረጃ አያድጉም። እዚያው በእንጭጩ እየተቀጩ ይሄዱና ሰላምና ፀጥታ ያብባል።

ስለ ፍትህ ሳስብ በልጅነት ጊዜየ አንድ የሆነ ነገር ዘወትር ትዝ ይለኛል። አንድ የማውቀው ሰው በሃይማኖቱ ምክንያት ይጨቆን ነበር። የከተማው የደርግ ባለስልጣናት በሆነ ባልሆነው እየከሰሱ ያሰቃዩት ነበር። ታዲያ ከእለታት አንድ ቀን የከተማው የቀበሌ ፍርድ ሸንጎ ይጠራውና ስለ ጥፋቱ ምንም ሳይነበብለት ለዛሬ 150 ብር ቀጥተንሃል ይሉታል። የሚያሳዝነው ይህ ሰው ለምን ብሎ አልጠየቀም። ፍትህ እንደሌለው ያምን ነበርና። በዚሁ መሰረት እዚያው ፍርድ ሸንጎው ፊት እንደቆመ የምስጢር ኪሱን ደባብሶ ብሮቹን አወጣና ወደ ሸንጎው ዘረጋ…..።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ፈንታሌ ውስጥ ስለተፈፀሙት ግድያዎች ኢሰመኮ ሪፖርት አወጣ

“ብሩን ለማን ነው የምከፍለው?” ብሎ በደከመ ቃልና በተሰበረ ልብ ስሜት ይጠይቃል።

የዚህ ሰው ልብ ቶሎ ብሎ ይህንን ቅጣት ከፍሎ ሄዶ በጎደለው እንደገና ደክሞ ሰርቶ ይህቺን ብር ለመሙላትና ለልጆቹ የሚሆነውን የወጉን ለማድረግ መጣር ነው። በግፍ የተነጠቃትን 150 ብር ለመመለስ ሳይደክሙ መስራት………።

ይህ ሰው የቀጣችሁኝን ብር ተቀበሉኝ ብሎ እንደዘረጋ  የመሃል ዳኛዋ አይኖች እንባ አመጡ….። የሚሰራው ግፍ ውስጥ አንጀቷን እያመሰ እንባን አስከቶሎ መፍሰስ ጀመረ…….። ራሷን መቆጣጠር አቅቷት ስቅስቅ ብላ ታነባ ጀመር። እየተንሰፈሰፈች አነባች……..። ሸንጎውና ታዳሚው ተከዘ…….።

በእውነት ይህቺን ሴት ዳኛ ያስለቀሳት ራሱ ፍትህ ነበር። ያ ፍትህ የሚባለው ረቂቅ ሰው ከህሊናዋ ፊት ቆሞ ወቀሳት……..። አነባች……..።በዚያ መድረክ ላይ የብዙዎች ህሊና ቆሸሸ።

ጎበዝ….. ፍትህ ያጣ ህዝብ ሁሉን ያጣ ህዝብ ነው። የቱንም ያህል የተፈጥሮ ሃብት ይኑረው፣ የቱንም ያህል ታሪክ ይኑረው፣ ያ ህዝብ ዛሬ የፍትህ ገበታው ከረከሰ እንደዚያ የሚያሳዝን ህዝብ የለም። በሃገራችን ውስጥ በመፈናቀል፣ በእስራት፣ በረሃብ የሚሰቃየው ህዝብ ፍትህ ጎድሎበታል። ስለመፈናቀል ስናስብ ብዙ ጊዜ የምንቆጥረው በአካል የተፈናቀለውን ብቻ ነው። የአካል መፈናቀል IDPs ወይም ከቀየው ተገፍቶ የተፈናቀለውን ህዝብ ስናይ ይህንን የአካል መፈናቀል እንለዋለን። ሁለተኛው መፈናቀል ግን የምኞት መፈናቀል ይባላል። የምኞት መፈናቀል ማለት አንድ ዜጋ በብሄሩ ምክንያት ሊሆን ይችላል የሚኖርበት አካባቢ ሲያስመርረው መሰደድን አጥብቆ የሚመኝና ብን ብሎ መጥፋትን እያሰላ የሚኖር ሰው ማለት ነው። በስነ ልቡና ጥናት የሰው ልጅ በሚኖርበት አካባቢ ይህ አካባቢ የእኔም ነው የሚል (Sense of belonging ) ሳይኖረው ሲቀር የሚኖረው ኑሮ የተፈናቃይ ኑሮ ነው። አካሉ እዚህ ቢታይም ልቡ ውጭ ነው ያደረውና። በስነ ልቡና ትምህርት ውስጥ Sense of belonging)    ለሰው ልጅ እንደምግብና ውሃ አንድ መሰረታዊ ፍላጎቱ ነው ይላሉ። ይህ መሰረታዊ ፍልጎቱ ሲነካ በምኞት ተፈናቅሎ ይኖራል። ጥናቶች እንደሚያሳዩት ወደ 70 % የሚሆነው የኢትዮጵያ ወጣት ብን ብሎ መሰደድን ይመኛል። የምኞት መፈናቀል ማለት ይሄ ነው። ሰው ፍትህን ከሰፈሩ ሲያጣው ያን ጊዜ  በሃሳብ  ተፈናቅሏል። ፍትህ ሲኖር ግን ዜጎች የትም ሄደው ለመኖር ዋስትና ስለሚሰጣቸው ዘና ብለው ይኖራሉ። የፍትህ መርበብ ደግሞ ሰላምን ያመጣል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የወልቃይት ጠገዴ ጠለምት አማራዎች የተጨፈጨፉባቸው በርካታ የጅምላ መቃብሮች መገኘታቸውን የጥናት ቡድኑ ገለጸ

በተወለድኩበት አካባቢ ፍትህና ዳኝነት በህዝቡ ልብና ባህል ውስጥ ትልቅ ቦታ አላቸው። አያይዙኝ፣ አቆራኙኝ፣በህግ አምላክ፣ የዳኛ ያለህ የሚባሉ ቃሎች ከአካባቢው በሰፊው ይሰማሉ። ለፍትህ ለህግ የበላይነት የሚመች ልብ ያለው ህዝብ ነው። በተመሳሳይ ለስራ ጉዳይ የሄድኩባቸው የደቡብና የኦሮምያ አካባቢዎችም እንዲሁ ለፍትህና ለህግ የበላይነት ጥማት ያለው ህዝብ ነው ያየሁት። ይህንን ህዝብ ከፍትህ በተጣላ መዋቅርና ስርዓት ልናሰቃየው አይገባም። ስርዓታዊና መዋቅራዊ ለውጦችን አምጥተን እነሆ ህዝባችን ከፍትህ ምንጭ ጠጥቶ ይርካ፣ እነሆ ከፍትህ ማእድ ቆርሶ ይጥገብ። እነሆ ሰላምና ደህንነቱ ይጠበቅ። ለዚህ ደግሞ ሁሉን አቀፍ የሆነ የሽግግር መንግስት ማቋቋምን ወቅቱ ይጠይቃልና ወደዚያ እንሻገር ከሁሉም በላይ የሃገር ጥቅምና ዘላቂነት ይቅደም።

እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.