ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ፤

ABN 1የአብን ጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ ኮሚቴ በአማራ ላይ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት (#AmharaGenocide) እያወገዘ መንግስት በተደጋጋሚ ጉዳዩን በቸልታ በመተውም ሆነ የጠያቂዎችን ድምፅ በማፈን ለችግሩ መቀጠልና መባባስ ከሚያደርገው አስተዋፅኦ እንዲታቀብና ህጋዊ ግዴታውን በመወጣት በአስቸኳይ እልባት እንዲሰጥ በጥብቅ ይጠይቃል፡፡ መላው የአማራ ሕዝብና አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን በጋራ በመቆም የዘር ፍጅቱ በዘላቂነት እንዲያከትም የሚያስችሉ እንቅስቃሴዎችን በማከናወን የዜግነትና የሞራል ኃላፊነታቸውን መወጣት ይኖርባቸዋል፡፡ ለዚህም ስኬት አንዱ መሰረታዊ ጉዳይ ጠንካራ የአማራ ተቋም መገንባትና ትግሉን ተቋማዊ ማድረግ መሆኑ ሊሰመርበት እንደሚገባና ሁሉም ከመሽኮርመም ወጥቶ በቆራጥነት እንዲነሳ ኮሚቴው ጥሪ ያስተላልፋል፡፡
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የጠቅላላ ጉባኤ ተወካይ ኮሚቴ ከድጋሚ የጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅት ጋር በተያያዘ የተለያዩ የጉባዔና የሪፎርም ዝግጅት ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱ ይታወቃል። የጉባዔ ቀንና ቦታ በመግለፅ ቦርዱ ወኪሎችን በታዛቢነት እንዲልክ የማሳወቅ ስራ ቢሰራም ጉባዔው ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረትና ተወካይ ኮሚቴውም ለማድረግ ዝግጅት በያዘበት ቀን ጉባዔው ይካሄድ ዘንድ ቦርዱ ለተወካይ ኮሚቴው እውቅና የሚሰጥ ምላሽ መስጠት አልቻለም፡፡
በተጨማሪም ለጉባዔው ስኬት ውይይቶች የተደረጉ ቢሆንም በተለያዩ የድርጅቱ ከፍተኛ የመዋቅር አካላት ውስጥ ያሉ አንዳንድ አመራሮች ከድርጅታችን መነሻ የትግል ግቦችና ከጠቅላላ ጉባያዔው በተቃርኖ በመቆም ጉባዔው በተቀመጠለት ቀን እንዳይካሄድ ከሚያደርግ አቋምና እንቅስቃሴ ሊመለሱ አልቻሉም፡፡ ሰኔ 12 ቀን 2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተደረገው አስቸኳይ የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባም ተገቢ ውጤት ያልመጣ ቢሆንም ተወካይ ኮሚቴው ከተወሰኑ የስራ አስፈፃሚ እና ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ጋር በአጭር ቀናት ውስጥ ውጤቱ የሚታወቅ ውይይት እንደገና ጀምሯል፡፡ በተጠቀሱት ምክንያቶች ሰኔ 18 እና 19 ቀን 2014 ዓ.ም ተጠርቶ የነበረው ጉባዔ ላልተወሰነ ጊዜ መሸጋገሩን ተወካይ ኮሚቴው በየደረጃው ላሉ የድርጅቱ አካላት ቀድሞ ያሳወቀ ቢሆንም ለሁሉም አባላትና ደጋፊዎች ማስተላለፍ አስፈልጓል፡፡
ተወካይ ኮሚቴው የደረሰበትን አጠቃላይ ውጤትና ልዩ ልዩ መረጃዎች ወደፊት የሚያሳውቅ መሆኑን እየገለፀ የሚከተሉትን መሰረታዊ ጉዳዮች ማስተላለፍ ይፈልጋል፡፡
1) ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፡-
በምርጫ ቦርዱ ውሳኔ መሰረት በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ጉባዔው እንዲካሄድ የድርጅቱ ማዕከላዊ ኮሚቴም ሆነ ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ስለመዘጋጀታቸው የሚገልፅ ምንም አይነት ማሳወቂያ ለቦርዱ ሳይደርሰውና ዝግጅትም እንደሌለ በድርጅቱ ኦፊሻል የፌስቡክ ገፅ በይፋ በተገለፀበት ሁኔታ፤ የጉባዔ ጥሪ ዝግጅቱን አጠናቆ ለቦርዱ ላሳወቀው በድርጅቱ መተዳደሪያ በደንብ አንቀፅ 11.1 መሰረት የድርጅቱ ከፍተኛ የስልጣን አካል በሆነው ጠቅላላ ጉባዔው አባላት ፊርማ የተረጋገጠ ውክልና የያዘው የጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ ኮሚቴውን የጉባዔ ጥሪ እውቅና አለመስጠቱ ተወካይ ኮሚቴው ትክክል ነው ብሎ አያምንም። በመሆኑም ተወካይ ኮሚቴው በድጋሚ በጠየቀው መሰረት የምርጫ ቦርዱ ያለውን ሁኔታ ከግምት ውስጥ አስገብቶ ጉባዔው በአጭር ቀናት ውስጥ እንዲካሄድ በማስቻል ለሰላማዊ ትግል እና ለዴሞክራሲ መጎልበት የበኩሉን አስተዋፅኦ እንዲያደርግ ተወካይ ኮሚቴው አጥብቆ ይጠይቃል፡፡
2) ለአብን ማዕከላዊ ኮሚቴ፣ ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን እና ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አመራሮች፡-
ጉባኤው ነባራዊ ሁኔታውን ባገናዘበ እና የጠቅላላ ጉባኤውን ፍላጎት ባከበረ መንገድ ባልተዘጋጀበት እንዲሁም ትክክለኛ ሪፎርም ባልተደረገበት መልኩ ድርጅታችን ካለበት ችግር ሊወጣና የሚገባው ድርጅታዊ ቁመና ላይ ሊገኝ እንደማይችል ከወዲሁ ትኩረት ሊደረግበት ይገባል፡፡ በጥቂት ግለሰቦች የግል ፍላጎት ምክንያት ከተገቢው አውድ በተለየ ሁኔታ የቅድመ ጉባዔው ሂደት ትክክለኛነት ባለው መልኩ ሳይቀጥል ቀርቶ የጉባዔና የሪፎርም ጉዳይ ስኬታማ ባይሆንና የፓርቲው ህልውና አደጋ ላይ ቢወድቅ የታሪክ፣ የህግና የሞራል ተጠያቂነቱ የሚያርፈው በድርጅቱ ስራ አስፈፃሚ፣ ማዕከላዊ ኮሚቴ እና ኦዲትና ምርመራ ኮሚሽን ውስጥ ባሉ አመራሮች ላይ መሆኑን በመገንዘብ አስፈላጊውን ሁሉ ገንቢ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ተወካይ ኮሚቴው ማስገንዘብ ይፈልጋል፡፡ በተጨማሪም የድርጅቱ የበላይ የስልጣን አካል በሆነው ጠቅላላ ጉባዔ መድረክ ማለትም በተቋረጠው የመጋቢት 11/2014 ዓ.ም ጉባዔ በግልፅ በተስተጋባው መሰረት በየደረጃው ባሉ መዋቅሮች የሚነሱ ጥያቄዎችና ጉባዔተኛው በፊርማው ውክልና በሰጠው ኮሚቴ በኩል በግልፅና በይፋ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን ያልተገባ ስም ከመስጠትና ከማደናቀፍ ተግባራቸው እንዲቆጠቡና የመፍትሔው አካል በመሆን ድርጅታዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ተወካይ ኮሚቴው በጥብቅ ያሳስባል።
3) በዞንና በወረዳ ለሚገኙ አመራሮች፣ ለጉባዔውና ለአጠቃላይ የድርጅቱ አባላት እንዲሁም ለደጋፊዎች፡-
ሳይጠናቀቅ የተቋረጠው የአብን 3ኛው ድርጅታዊ ጠቅላላ ጉባዔን እንደገና በመጥራት ጉባዔ ተካሂዶና ተገቢው ሪፎርም ተከናውኖ ብዙ ዋጋ የተከፈለለት ድርጅታችን ትክክለኛ አቋሙ ላይ እስኪገኝ ድረስ የአብን ጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ ኮሚቴ ትግሉን እንደሚቀጥልና የውይይት ውጤቱንም ሆነ ሌሎች ዝርዝር ጉዳዮችን በተመለከተ በቅርቡ እንደሚያሳውቅ ተገንዝበው ሁሉም መርህን መሰረት ባደረገ መልኩ ትግሉን በተለመደው ቁርጠኝነትና ፅናት እንዲቀጥሉ ተወካይ ኮሚቴው ያሳስባል።
አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፣ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!
ሰኔ 18 ቀን 2014 ዓ.ም
አዲስ አበባ፣ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ
የአብን ጠቅላላ ጉባዔ ተወካይ ኮሚቴ
ተጨማሪ ያንብቡ:  ከብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት በወቅታዊ ሀገራዊና ቀጠናዊ፣ የደህንነትና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ የተሰጠ መግለጫ

Leave a Reply

Your email address will not be published.