መንግስት ማንነትን መሰረት አድርገው የሚሰነዘሩ ጥቃቶችን ለማስቆም ተገቢውን እርምጃ በመውሰድ አለበት

“በድንገት መጥቶ ህዝብን ከሚያጠቃው እኩይ አካል እኩል ዜጋውን የመጠበቅ ግዴታ ኖሮበት የማይጠብቀው መንግስት ተጠያቂ ነው”

የማያባራ ስቃይ፣ የማይረጋጋ ነፍስ፣ ጽልመት የዋጠው የሰቆቃ ኑሮ፣ የማያሳርፍ ጭንቀት ተሸክመው እጅግ መራር ህይወትን እንዲገፉ የተፈረደባቸው ወገኖቻችን ዛሬም የሰው አውሬ ስላገኛቸው እንዲሁም ጠባቂ ስላጡ ልባችን ክፉኛ በሃዘን ተሰብሯል።

የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) መንግስት ማንነትን መሰረት አድርገው የሚሰነዘሩ ጥቃቶችን ለማስቆም ተገቢውን እርምጃ በመውሰድ ዜጎችን ከአሰቃቂ ጭፍጨፋ የመጠበቅ መንግስታዊ ግዴታውን እንዲወጣ በተደጋጋሚ ሲያሳስብ እንዲሁም መፍትሔ ያላቸውን ምክረ ሐሣቦችም ሲያቀርብ ቆይቷል። ሆኖም መንግስት ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ ማሳሰቢያዎችንም ሆነ ምክረ ሀሣቦቻችንን ለመቀበል ምንም አይነት ፍላጎት አላሳየም።

የህግ የበላይነትን የማስከበር ሃላፊነቱም ከዕለት ዕለት ጥያቄ ውስጥ እየገባ መምጣቱ በብርቱ አስግቶናል።

በትናንትናው ዕለት ሰኔ 27 ቀን 2014 ዓ.ም በቄለም ወለጋ አካባቢ በንጹሀን ዜጎች ላይ የተለመደ ተመሳሳይ አሰቃቂ ጭፍጨፋ መፈጸሙ እጅግ አሳዝኖናል።

መንግስት፣ ታጣቂ ሀይሎች ላይ እርምጃ እየወሰደ መሆኑን ተከትሎ እየሸሹ የነበሩት ታጣቂዎች የፈጸሙት እንደሆነ ገልጿል። መንግስት እንዲህ አይነት እርምጃዎች ሲወሰዱ ታጣቂ ሀይሎች በሽሽት ላይ ምን አይነት ጉዳት ሊያደርሱ እንደሚችሉ የሕወሓት ወራሪ ሃይል ከአማራና ከአፋር ክልል ሲወጣ ከፈጸመው እኩይ ድርጊት በመማር ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ሲገባው ሆነብሎ(በተባባሪነት)/በቸልተኝነት/በተለያዩ በአቅም ማነሶች እንዲሁም የእኩይ ሀይሉ ተባባሪዎች በመንግስት መዋቅር ውስጥ መሰግሰጋቸው እና የዜጎችን ነፍስ ለመታደግ የሚያስችሉ ተግባራትን በቁርጠኝነት ባለመተግበሩ ተጠያቂ ያደርገዋል።

መንግስት በተለይም በወለጋ አካባቢ በዚህ ደረጃ ለምን የጸጥታ ችግሮችን መቆጣጠር እንደተሳነው ለሕዝብ በግልጽ የማሣወቅ ግዴታ ያለበት ከመሆኑም በተጨማሪ ዘላቂ መፍትሔዎችን ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር መስራት እንዳለበት አጥብቀን ማስገንዘብ እንወዳለን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  “ሕወሃትን ለመዋጋት የኢትዮጵያ ሕዝብ ቀስቃሽ አያስፈልገውም!” ከአገር አድን ግብረኃይል የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ

ይህ መፍትሄ የጊዜ ገደብ ወጥቶለት አካባቢውን ከመሠል ጥቃቶች በምን ያህል ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ ነፃ እንደሚያወጣ በይፋ በመግለጽ መንግስት ለዜጎች ደኅንነት መጠበቅ ምን ያህል ቁርጠኛ እንደሆነ እና መንግስታዊ የማስፈጸም አቅም እንዳለው ሊያሳይ ይገባል። ይህን ማድረግ የማይችልና ዛሬም አድበስባሽ ሆኖ መቀጠል ካሰበ አካባቢውን የመቆጣጠር አቅምም ሆነ ፍላጎት እንደሌለው ያሳብቅበታል።

ከመንግስት የደህንነት ክፍተቶች ባሻገር በአካባቢው የሚኖሩ ዜጎች ከአብራካቸው የወጡ፣ አብረዋቸው ለረዥም ጊዜ የኖሩ እና በጋብቻ፣ በባህል፣ በእምነት፣ ወዘተ… የተጋመዱ ወንድምና እህት ዜጎችን የመኖር መብት ለማስከበር አብረው በመቆም፤ ከዚህ አይነቱ ዘግናኝ ጭፍጨፋ በመከላከል ሰብዓዊ እና ኢትዮጵያዊ እሴቶችን እንዲያስቀጥሉ እንዲሁም በማህበረሰብ መካከል የተፈጠረ ጥላቻ እንዳልሆነና ደም የጠማቸው ግፈኞች እኩይ ተግባር መሆኑን በተግባር እንዲያሳዩ አበክረን እንጠይቃለን፡፡

በመጨረሻም ፓርቲያችን አንደኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ መቆየቱ የሚታወቅ ሲሆን በቅርብ በዚህ እና ሌሎች ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም በስፋት ያሳውቃል፡፡

289607297 324046126605564 713037739839701108 n

 

 

#ኢዜማ

1 Comment

Leave a Reply

Your email address will not be published.