አታውሩልኝ ሌላ (አሁንገና ዓለማየሁ)

አታውሩ ሌላ

ይልቅ አውሩልኝ/ ስለ መንደሬ/ ስለ ጎጤና/ ስለ ጓሮዬ

ከሱ በስተቀር / ሌላ ሌላ ግን/ ፈጽሞ አይስማ/ ይሄ ጆሮዬ

እስኪ ዙሩልኝ /አንድ ሺህ ጊዜ /ያንኑ ጓይላ

እኔም አዙሮኝ/ ድፍትፍት እስክል/ የ-እን-ግ-ሊ-ላ

እስኪ ውረዱ አስወርዱኛ ያንን ረገዳ

ስብር እስከሚል ስብር-ብር-ብር-ብር ያጥንቴ አገዳ

እስኪ አንዘፍዝፉኝ ተንዘፍዘፉና በዚያ እስክስታ

ወባ እንደያዘው ዝልፍልፍ ብዬ እስክወድቅ ማታ

አትቀይጡብኝ ሌላውን ወሬ ሌላ ጨዋታ

ያችኑ ጎጤን ያሳይ ኢቲቪ ፋና እና ዋልታ

ያንኑ ጥለት ልየው በቀሚስ ልየው በኩታ

ያንኑ ምግብ ልየው በሰፊው ሞልቶ ገበታ

የሌላ ወሬ አይደባለቅ

በሌላ ነገር አይጨማለቅ

የጓሮው ብቻ ያ የመንደሬ

ሲነጋም ሲመሽ ይነገር ወሬ

ደስ ደስ ይበለኝ ትጥበብ ሰፈሬ

ከክልል በታች ክልል ከልሎ ይከለል አጥሬ

ከመቶ ሚልዮን ቅንስንስ ብሎ አንድ ይሁን ቁጥሬ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጄ/ል ክንፈ ወንድም የሆኑት አቶ ኢሳያስ ዳኘው ለቀረበባቸው ክስ መቃወሚያቸውን አሰሙ

Leave a Reply

Your email address will not be published.