አሳማ! – በላይነህ አባተ

ወገኑ ተወስዶ ሲታረድ በካራ፤
ድምጡን ጥፍት አርጎ የሚውጥ ሙዳ፣
እምብርት ማተብ የለው ሰው መሳይ አሳማ፡፡

ዓይኑ እያስተዋለ ጆሮው እየሰማ፣
ዘመድ ተሰውቶ ጥብስ ወጥ ሲሰራ፣
አፍንጫው አሽትቶ ለኻጩ እየወጣ፣
አፉን ተምግብ ተክሎ ያገኛል ደስታ፣
ደመነፍስም ፍቆ የዛሬው አሳማ!

የዘመኑ አሳማ እጅጉን እርኩስ ነው፣
እንኳን የወንድሙ ሥጋ ቅፍፍ ሊለው፣
የራሱም ፍሪንባ ተቆርጦ ቢሰጠው፣
ተስገብግቦ ሳስቶ እሚዘነችር ነው፡፡

መኖ ተጣሉለት ወደ አፍ የሚገባ፣
ዓይኖቹ እማያዩ ጆሮው የማይሰማ፣
ተፊቱ ደም ቢፈስ ቢከመር ሬሳ፣
ጩኸት ቢበረክት ወገን ቢያፈስ እንባ፡፡

ሊያርዱና ሊበሉ ለነገ ሲያደልቡት፣
ወንድም እህቶቹን አርደው ሲመግቡት፣
ምንም ሳያቅማማ ዝም ብሎ የሚውጥ፣
እንደ ጉንዳን ፈልቷል ተአገሬ ምድር ውስጥ፡፡

እንኳን ቅዱስ ፍጡር እርኩሱን አሳማ፣
ተጭራቅ ታራጆች ነፃ የሚያወጣ፣
በጫካው በዱሩ ጎራው የሚል ጀግና፣
አስበልቶ በልቶ መኖር የሚዳዳ፣
ደም ፈርስ ተመግቦ እጅግ የከረፋ፣
አገሬን ወሯታል እምብርት አልባ አሳማ፡፡

ሆዱ እስተሚቆዘር አብልተው ሲልኩት፣
እንደ አበደ ውሻ ቻዝ ብለው ሲያዝዙት፣
የራሱን ነፃ አውጪ ለሆዱ እሚያሳድድ፣
የማታ የማታ ግን እርሱም የሚታረድ፣
አሳማ በርክቷል በጥቅም ያበደ ጉድ!

ዘሩ ጥፍት ቢል ታርዶ በእለት በእለት፣
ደንታ የማይሰጠው ቢነግሩት ቢያስረዱት፣
አሳማ በርክቷል ለቁጥር የሚያታክት፡፡

ያለፈውን ትውልድ አያይ የወደፊት፣
ታህዮችም አንሶ ሰርዶ አይብቀል ታሉት፣
ደጅ ሲጠና ያድራል ወገኑን ለሚያርዱት፣
ሆደ ኬሻ አሳማ ምን ህሊና አግዶት፣
ፍርፋሪ ልፋጭ ተወረወሩለት፡፡

ማተብ ያጠለቀ ሕዝብ እንደሚረዳው፣
አገር መንደር ሰፈር ቅዱስ እሚሆነው፣
ወገን አሳርዶ ልፋጭ ተሚበላው፣
ተርኩስ ጥንብ አሳማ ሲጠዳ ብቻ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ተጠየቅ (ዘ-ጌርሣም)

በላይነህ አባተ ([email protected])
ነሐሴ ሁለት ሺ አስራ አራት ዓ.ም.

Leave a Reply

Your email address will not be published.