መንጋነት እና ፓለቲካል በግ’ነት ተነጣጥለው አይታዩም ( አባታጠቅ  ምንዳሁነኝ )

ያለፉትን አራት ዓመታት የመራውን ግለሰብ አብይ አህመድን ብንመለከት በሕዝብና በአገር ስም የሚሰጠውንም ሆነ በብድርና በእርዳታ የሚገኘውን ገንዘብ እንደ ግል ሃብቱ ሲበትን፣ለምን  እንዲህ ይሆናል ብለው የጠዬቁትን ምን አገባችሁ እያለ ሲሳደብና ሲያንጓጥጥ ማዬቱ የተለመደ ነው

” ሰው ፖለቲካል እንስሳ ነው ።” ማህበራዊ ሳይንሱ እንዲህ ያስተምራል ። ቀጥታ  ” በግ ነው ፡፡ ” አይልም ፡፡ ማህበራዊ ሣይንሱ ፡፡ ቀጥታ ” እንስሳ ነው ፡፡ ” ያለው ዳርዊን ነው ፡፡ ዳርዊን በግልፅ ” ሰው ዛሬ ጭራ አልባ ከመሆኑ በፊት ባለጭራ ዝንጀሮ ነበር ፡፡ ” ነው ያለው ፡፡ የሱን ሃሰብ በበኩሌ አላራምድም ። አለምንበትማ ፡፡ ” ሰው ፖለቲካል እንስሳ ነው ፡፡ ” የተባለው ፣ ” ማህበራዊ እንስሳ ነው ፡፡ ” ከተባለ በኋላ ነው ፡፡ ያው ተቀራራቢ ትርጉም ነው ያላቸው ፡፡  ይኽንን ለመረዳት ፤  በአንድ ሰው ፤ የእውነትም ሆነ የቅጥፈት  ትርክትና ተሥፋ ኋላ ብዙዎች  ፍሬ ለማፍራት ወይም ሙጃ ለማጨድ የፖለቲካ ዓላማን ተገን አድርገው ፣ በሚንቀሰቅሷቸው ግለሰቦች ተገፋፍተው በየጊዜው ለአብዮት ና ለለውጥ  የሚሰለፉ የበዙ ሰዎችን  ማስተዋሉ  በቂ ነው ።

የሴራን ፖለቲካንም አሳምሮ  የሚያውቅ ይኽንን እውነት በቅጡ ይገነዘባል ብዬ አምናለሁ ፡፡ በልምድ የደረጀ ፤ ማንኛውም ኤሌት ሆነ ልሂቅ ፤  በግለሰብ ደረጃ ሠናይ ወይም እኩይ  ምናባዊ ሃሳብ ይዞ ፤ የተደበቀ ግብን ዓልሞ ፤ ፖለቲካዊና ኃይማኖታዊ ካባም ደርቦ ወይም ሌጣውን ፤ በሺ የሚቆጠሩ ዝቅተኛ ንቃተ ህሊና ያላቸውን ሰዎች ህሊና ጨምድዶ በመያዝ ፤  ላቀደው ዓላማ ከጎኑ  በማሰለፍ ፣ አጥፊ ወይም አልሚ መንጋ ሊፈጥር ይችላል ፡፡   “የሰውን ፖለቲካዊ እንስሳነትን በመጠቀም  ። ”

እኔም በዚህ ሃሳብ እሥማማለሁ ።  ግን ፣ ግን  ” ሰው ፖለቲካዊ እንስሳ ነው ። ” ከተባለ ፣ ሰው ልጅ ፣ ከእንስሳ መካከል አንዱን መምሰል ይኑርበታልና በዛሬ በዓለም እና  በኢትዮጵያ ተጨባጭ የፖለቲካ እውነታ አኳያ የዓለምን አሳብያን  አመለካከት በመመርኮዝ ፣ ጥቂት የማንለው ፣ የዛሬው    ሰው ”  ወደ በግ ባህሪ ያዘነበለ ፖለቲካል  እንስሳ  እየሆነ መጥቷል ። ”  ። በማለት የምንደመድምበት አጋጣሚዎች እንዳሉ ይታወቃል ፡፡ ራሱ ሰው በመንጋ በመንቀሳቀስ  የፈፀማቸውን እኩይ ድርጊቶች ለታሪክ  የበቁ እና ተጽፈው የተቀመጡ  ናቸው  ፡፡ በእውነቱ የበዛው ሰው ለምን በራሱ አእምሮ እነደ ማይማር ግራ ያጋባል ፡፡ አብሶ በከተማ ያለው ፡፡

ሃሳብያን እንደሚስማሙበት እና ሥለ ሰው ባህሪ የሚያጠኑ ሊቃውንት እነደሚናገሩት ፣  ከ10 ሰዎች አንዱ ለመሪነት የተፈጠረ ሰው ነው ። አንዱ ደግሞ ፈላስፋ ና ነገን አመላካች ደራሲ ፣ ከዓላማው ዝንፍ የማይል ኃቀኛ ምሁር ።     ለሀገሩ ሥለፍቅር  ነፍሱን ሳይሰስት የሚሰጥ ወታደር ፣ ለሃቅ ሟች እና ተሟጋች ጋዜጠኛ  ( እንደ ባዓሉ ግርማ ፣ ታዲዎስ ታንቱ ፣ ተመስገን ደሳለኝ ወዘተ ። አይነት ማለት ነው ። ) በጥቅም ፣ በሆድ የማይገዛ ፣ ከራሱ ጋራ ሁሌም ተከባብሮ የሚኖር ሰው   ሲሆን ፤ የተቀሩት 8ቱ ግን ተነጂዎች ናቸው ።  በተራ ቁጥር 1 ለመነዳት የተፈጠሩ ። የምላሰኛው ፣ የአጭቤው ፣ የጨካኙ ወይም በተቃራኒው ፤  የአርቆ አስተዋዩ ፣ የታገሹ ፣ የሩህሩሁ ፣ በቀና መንፈስ የተሞላው መሪ ተነጂ ። …

ይኽንን እውነት ህዝባችን የሚሉትን እነ ደብረፂዮን ና ተነጂውን ህዝባዊ ማዕብል የተባለውን መንጋ  በማየት  መገንዝብ ይቻላል

መንጋው ፣ በዛሬው ፣ የጥፋት ሰልፍ ለምን እንደተሰለፈ ቢጠየቅ አንዳችም የሚያረካ መልሥ የሚያመልሥ ከመንጋው ውስጥ አታገኝም  ።  ” ጎደኞቼ ሁሉ ተገደው እና ወደው መሣሪያ ሥላታጠቁ ፣ እኔም ወጣት በመሆኔ ፣ እንደእነሱ መሆን ፈለኩ ። ደሞም አማራጭ የለኝም ። ” ሊል ግን ይችላል ፡፡

እንዲህ ዓይነቱን በፍላሎት ብቻ የሚነዳ የወጣት  ሥብሥብ  ” ፖለቲካል የሰው በግ መንጋ ! ” በማለት ብንበይነው  ። የተሳሳትን አይመስለኝም ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  “የትኛውም የሥራ ፈጠራ የሚመነጨው ከችግር ነው” - ከፎርጂዱ ዶ/ር ኢ/ር ሳሙኤል ዘሚካኤል ጋር የተደረገ ቃለምልልስ

እንደምታውቁት በጎች አንዱ በግ በሚጎዝበት አቅጣጫ ግር ብለው የመጎዝ እንጂ አማራጭ መንገድ በማየት በየፊናቸው አይጎዙም ። በመሆኑም መሪውን በግ ከኃላ ተከትለው የበዙ በጎች እየተጓዙ ፤ የሰው ማሳ ውሥጥ ዘው ብለው በመግባት ወይም የሰው ሥጥ ላይ በመረባረብ በደመነፍስ የሚያጠፉ ናቸው ።  ብዙውን ጊዜ በልምጭና ዱላ ቢሸነቆጡም የሚታረሙ አይደሉም  ። ተመልሰው ያጠፋሉ ። ሺ ጊዜ ወደ እዛ ሥፍራ ይመላለሳሉ ። መሪያቸው የቀመሰውን ምግብና ቦታውን ሥለማይረሳ የማሥታወስ ችሎታው ከፍተኛ ሥለሆነ እነዚህን በጎች ሺ ጊዜ እየወሰደ ያሥቀጠቅጣቸዋል ።

ይኽ የዘወትር የበጎች ገጠመኝ የበግ ፖለቲካን  ምንነት አሣምሮ የሚገልፅልን ክሥተት ነው ። እርግጥ ነው ። መንጋውን እንግልትና ወከባ ከሌለበት የግጦሽ ክልልም እየመራ የሚያደርስ እውነተኛ  መሪ በግ አለ ። ይኼ በጎችን በበግ የመምራት አውዳሚ ፖለቲካ ፣ ከእየሱስ አሥተምህሮ ጋር የሚጋጭ ነው ። በጎች በመልካም እና ቅን እረኛ ሊመሩ እንደሚገባቸው ኢየሱስ በሐዲስ ኪዳን ማስተማሩን አትዘንጉ ።  ( የዮሐንስ ወንጌል ም 10 ፤ 1_15 አንብቡ )

በመንጋነት ውስጥ ፣ ሰው ፖለቲካል በግ ነው ። በዚህ ፀሐፊ አተያይ ። ይኽ ፀሐፊ ” ሰው ፖለቲካል በግ ነው ። ” በማለት በብዕር ሥም ለመፃፍ የተገደደውም ከብዙ ተነጂ በጎች ከሚደርስበት ማሥፈራርቾ ፣ ስድብ ፣ የሥዶች ፉተታ ነፃ ለመሆን በማሰብ ነው ። … ማለትም ማንኛውንም ክፉ ቃላት ፣ ቆሻሻ መድፋት ፣ መንጋዊ  ቅርሻት ተለውሶ ቤተሰቡን ለመለወስ ባለመፈለጉ ነው ፡፡ በእውነቱ በመሳቅ ስድቦችን  ለማሥተናገድ የብዕር ሥም ይመቻል ። ( በዓለም ላይ  አንቱ የተሰኙ ፀሐፊያን በብዕር ሥም ይፁፉ ነበር ። በኢትዮጵያም የበዙ በሳል ፀሐፊያን በብዕር ሥም ይፅፉ  እንደነበር ይታወቃል ። ዛሬም በብዕር ሥም የሚፅፉ አሉ ። )

ወዳጆቼ ፤ ሰዎች ሆይ ! ሰው ፖለቲካል በግ ለመሆኑ አገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ እውነታዎችን በመጥቀስ የሰውን የፖለቲካ በግነት በይበልጥ  ማሥረዳት ይቻላል ።

ከኢትዮጵያ ያለፉት 40 ዓመታት  የፖለቲካ ተመክሮ በመነሳት  የመንጋነትን  የውድመት ጉዞ ፣ በወፍ በረር ለምን አላሥቃኛችሁም  ፦

በ1967 ዓ/ም ደርግ የሚባል አውራ ፖለቲካል በግ ተነሳ ና ኢህአፓ የተባለውን አውራ ለመሆን የሚገዳደረውን ፖለቲካል በግ ግድሎና አሰዶ በማጥፋት ፤ በጉልበት   የአገሪቱ ብቸኛ  መሪ የሆነው ፤ ኢህአፓ ወጣቱን በግራ ዘመመ ፖለቲካ እያዋከበ ፤ የኮሚኒሥት አረቄ እያጠጣ አሥክሮ ሲያበቃ “እናቸንፋለን ! እና እናሸንፋለን ! ” እያሰኘ በደርግ  ፊት መንጋውን በሚመሩት አውራ በጎች ስሜታዊነት እና ችኩልነት እርስ በእርሱ ስለ ተባላ ነው ። በዛ ላይ በደርግ ውስጥ ሰርገው የገቡትን  የኢህአፓ አባለት ደርግን ለምሳ ሲያስቡት ደርግ ነቃና ቁርስ አደረጋቸው ።

ደርግም ዘግይቶም ቢሆን ለኢምፔሪያሊዝም ራት መሆን አልቀረለትም ። ዓለማቀፋዊውን ፖለቲካ የሚመሩት ሁለት አውራ በጎች በታላቁ ቀዝቃዛ ጦርነት ተፋልመው አንዱ ወገን ማለትም በጎርቫቾቨ የዋህነት የሚደገፈው  የአሜሪካኑ ጎራ ፣ ሶቬት ህብረት በመፈራረስ ድልን ተቀናጁና  የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝም  ብቸኛው አውራ ፖለቲካል በግ ሆኖ ብቅ አለና ደርግን ረጋ ብሎ አጣጥሞት ተደላድሎ በወያኔ ውሥጥ ተኛ  ።

በዓለም ፖለቲካም ፣  የአሜሪካን ኢፔሪያሊዝም  በቀደደው መንገድ የሚጓዙ እንጂ ፤ በሶሻሊዝም ጎራ የሚጎዙ እየከሰሙ መጡ ። ሰሜን ኮርያ ፣ ኩባ ፤ ለየት ያለ ሶሻሊዝም የምትከተለው ቻይና እና 17 አገር ከሆነችው ከቀድሞው ሶቬት ህብረት  በታላቅ አገርነት የምትታወቀው ሩሲያ ብቻ ራሳቸውን የቻሉ ተገዳዳሪና አውራ ፖለቲካል በግ ሆኑ ።

የሶቬት ህብረት መፈረካከስ ጦስ ለደርግም ተርፎት በአሜሪካ ሤራ ወያኔ የተሰኘ ፖለቲካል አውራ በግ  የኢትዮጵያ መንግሥት ሆነ ። እናም ለ 27 ዓመት ይኽቺን  አገር ከኋላው ብዙዎቹን ፖርቲዎች ” ባኣኣኣ ! ” አያሰኘ ፣ መራ ። የመንጋነት ተምሳሌት የበግ መንጋ መሆኑንን ሥትገነዘብ ፣ ነገርየው ይገባሃል ። በቀላሉ የበግ ፖለቲካል ኢኮኖማን ትገነዘባለህ  ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከፈረሱ ጋሪው - አበበ ገላው

ከ27 ዓመት በኋላ ደግሞ ፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ፣ በተለያዩ አውራ የፖለታካ በጎች ሥር  መሠለፉ ታወቀ ።   የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝምን አላሥበዘብዝ ብሎ ብቻውን ሲያግበሰብስ የነበረውን የወያኔ ከበርቴን ከመንግሥትነት አሽቀንጥሮ ለመጣል ለ6 ዓመታት ህቡ እና ግልፅ ትግል አደርጎ ወያኔንን ከምኒልክ ቤተ መንግሥት  ለማባረር  የአለም አውራ በጉ አሜሪካ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል ። በአሜሪካ የሚኖረው ተውልደ ኢትዮጵያዊም በአሜሪካ ውሥጥ ፣ ወያኔንን በተቃውሞ ፤ በዓለም ህዝብ ፊት አንገቱን እንዲደፋ ሲያደርግ ፣ ለአገር ውሥጥ  ተቃዋሚ ደግሞ የገንዘብ ድጋፍ በህቡ ያደርግ ነበር   ።  እናም በህቡ ሤራ በኢህአዴግ ውሥጥ አንጃ በመፍጠር ፣ ትህነግ ከሥልጣን እንዲገለል ለማደርግ የተቻለው በአሜሪካ ሥውር እጅ ነው ። ማለት ይቻላል ፡፡

ከዛሥ  ? የአለም  አውራ ፖለቲካል በግ የሆነው የአሜሪካ ኢምፔሪያሊዝም  አዲስ የለውጥ መንግሥት በኢትዮጵያ በመምጣቱ በጅምሩ ተደስቶ ነበር  ። ሲቆይ ግን ብልፅግና የተሰኘው የለውጡ አውራ በግ ፖለቲካል ኢኮኖሚ እየሸከከው መጣ ። ኢትዮጵያን ላለ ማስበዝበዝ መቁረጡ  አበሳጨው ። ( መሱንናን ያለመዋጋቱ እና በውስጡ ቦና ፓርቲዝምን መፍጠሩን ግን ልሸሽግለት አልችልም ፡፡ ) ከልክ በላይ የሆነው ፣ የህዝቡ ድጋፍ ወይም አውራውን የመከተል ሁኔታም አላማረውም እናም  ጥቅሙን  ለማሥጠበቅ የኃይል ሚዛን ባላንስ ማድረጊያ ዘዴ ቀየሰ ። ወያኔንን ትግራይ እንዲመሽግና ወታደራዊ አቅሙን እንዲያጎለብትና ተፎካካሪ አውራ በግ እንዲሆን አደረገው ። ማለትም በሚሊዮን የሚቆጠር ከኋላው የሚግተለተል በግ እንዲያፈራ አደረገ ።

ከዚህ በተጎዳኝም በአራቱም መዓዘን ኢትዮጵያን ውጥረት ውሥጥ የሚከቱ የጎሣ ፣ የነገድ ፣ የቋንቋ የበግ አወራ ፖለቲከኞችን በህቡ ማጠናከሩን ተያያዘው ።

ወዳጄ  ” ግብፅ ናት ገንዘብ አቀባዮ ፤ ” ብለህ ብታምንም ገንዘቡ የአሜሪካን ነው ። አሜሪካ ለግብፅ በየአመቱ ቢሊዮን ዶላሮች  እርዳታ እንደምትሰጥ ተገንዘብ ። አሜሪካ እና  ኢንግሊዝ  የግብፅ  ወዳጆች ናቸው  አራት ነጥብ ( ። )

በዓለም ላይ እነዚህ ኃያላን አገሮች አውራ በጎች ናቸው ። ያውም ድምፅን በድምፅ የመሻር መብት ያላቸው የዓለም ንጉሶች ። በእርግጥ ቻይ ና እጋሯ ሩሲያም ድምፅን በድምፅ የመሻር መብቱ አላቸው ። እንደውም ” ድምፆችን በድምፅ የመሻር መብት አላቸው ። ”  ማለት ነገሩን በይበልጥ ያሥረዳል ። ምሳሌ ፦  እንበልና 100 የአፍሪካ አገሮች  ”  እነዚህ  ዓለም አቀፍ  ወንጀለኞች እና አሸባሪዎች  ናቸው ። የወያኔ መሪዎች  ይታሰሩ ።    ” ብለው  ለተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በፅሑፍ የውሳኔ ሃሳብ ቢያቀርቡ ፣  ከነሱ አንዱ ” ወንጀል ቢሰሩም ፣ አይታሰሩም ። ” ካለ  አይታሰሩም ።

ለምን ቢሉ ? አፈሪካውያን ብቻ ሳይሆኑ የኒኩለር አረር ያልታጠቁ ሁላ ፣ ሸክላዎች እንጂ ብረት አይደሉም ።  ” ለሃምሳ ጋን አንድ አሎሎ ። ” ነው ነገሩ ። ለመሆኑ የኒኩሊየር አረር ከያዘ  ፣ የፖለቲካ አውራ በግ ጋር ማነው እሰጥ አግባ የሚጀምረው  ? ዩክሬን እና ደጋፊዎቿን አሜሪካን እና አውሮፖን አታይም  እንዴ ?  አንድ ሩሲያ ናት በኒኩለር እየሥፈራራች ገትራ የያዘቻቸው ። ( ይኽንን ጦርነት አሜሪካ ቤንዚን ለምን እንደምታርከፈክፍበት ይገባሃል ? ለጥቅሟ ሥትል ነው ። ለአውራዎቹ  የፖለቲካል በጎች ፣ ለ1% ቱጃሮቿ ብልፅግና ሥትል ነው ። ለንግድ ነው ። ያውም ደጎስ ያለ ትርፍ ለሚያስገኝ ትርፍ ።  ሌላ ዓላማ ያላት እንዳይመስልህ ። ” ለዴሞክራሲ  ፣ ለቅብርጥስዬ ፣ ለምንትስዬ ለሰብዓዊነት … ” ይሉሃል ። ወዳጄ አትጃጃል ፤ ጅላንፎ አትሁን  ።  ዴሞክራሲ ልባስ ነው ። ፍሬ ነገሩ ጥቅም ነው ። ፍሬነገሩ ሩሲያን ማዳከም ነው ። የታይዋንም ጉዳይ ቻይናንን ለማዳከም  የአሜሪካ ሲአይኤ የቀየሰው መንገድ ነው ። ጦርነት እንደሚያከስርም እንደሚያተርፍም ሲአይኤ አሳምሮ ያውቃል ። በዓለም በተነሱ ጦርነቶች ሁሉ ግን አሜሪካ  ስታተርፍ  እንጂ ኪሳራ ሲያጋጥማት አላየንም ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ታሪክን የኋሊት፤ የአቶ መለስ ድንጋጤ! (አቤ ቶኪቻው)

እንግዲህ ይኽ በዓለም አውራ በጎች የሚዘወረው ፖለቲካ    በየፈርጁ እየወረደ እና እየተመነዘረ ለየአህጉሩ ሁሉ ይደርሳል ። አፍሪካም በአውራ የፖለቲካ በግ በሆኑ ፖርቲዎች በኩል ፣እንደመንግሥታቸው ጥንካሬ እና ድክመት የሚወሰን ” የአድርግ ። አታድርግ ። ” መልዕክት  በእንዚህ ኃያላን  አውራ ፖለቲካል በጎች ይደርሳታል ። ምርጫዋ ትዕዛዛቸውን  ተከትሎ ከእነሱ ኋላ ፣ ኃላ በመሄድ ወደ ተሻለ ብልፅግና ወይም ወደ ከፋ ውድቀት  መድረስ በቻ  ነው ።

“ግን፣ግን ማህሉን ቢመርጡሥ ? ” ወዳጆቼ ማህል ብሎ ነገር የለም ። በሁለት ኃያላን መካከል ሆነህ የገመድ ጉተታ ዳኛ መሆን አትችልም ።  ወደ አሸናፊው ለማዘንበል የኃይል ሚዛኑንን ገምግም ። የቱ ያዋጣኻል ? እንደ እባብ ካብ ላይ ወጥተህ ተመልከት ። እንደ እርግብም ሰማዩን እየቀዘፍህ አሰላሥል ፤  እናም በጥበብ ከኋለህ የሚከተሉህን በማስተዋል ለማሻገር ድልድይህን ሥራ ። የድልድዩን መሠረትም ጥልቅ አድርግ ።

ይኽ ማለት ምን መሰለህ ? ለዚች አገር መሪ ስትሆን የዚች አገርን ህዝብ ንቃተ ህሊና ጠንቅቀህ ማወቅ አለብህ ። አብዛኛው ሰው ፣በኑሮው እርካታ ስለሌለው እጅግ ተሥፈኛ ነው ። በመሆኑም አንድ ንቃተ ህሊናው ደረጃ በከፍታ ላይ ያለ ሰው ፣ የቋንቋን ፓለቲካ ተገን በማድረግ በመንጋው ንቃተ ህሊና ዝቅተኝነት ተጠቅሞ ” መና ከሰማይ አውርድልሃለሁ ። ”   ባይለው እንኳ ፣ በትንሽ ፍራንካ ዲንጋይ ሊያስወረውርብህ ይችላል ። …

ይኽንን እንዳያደርግ የሚያሥችልህ አንድ  ተሥፋ  እንዳለህ ግን እወቅ ።  እሱም  ” ዘረኝነትነት ፣ ቋንቋ አምላኪነት በዘወግና በጎሣ ብሎም በወንዝ መቦደን የአገርህ ሰው ትቶ ፣ በሰውነቱ እንዲደራጅ  ማድረግ ነው  ።  ” ክልልን አጥፋ ። ሌላ ሥያሜ ሥጠው ።ክልል ቃሉ  በራሱ አትድረሱብኝ የሚል ነው ፡፡

አትድረሱብኝ እያልክ  ” ኦሮምኛ ተናጋሪ በመሆንህ ብቻ ፣ ባልፈጠርከው መሬት ፤ ፖለቲካው በወሰነልህ  ውሳኔ አስገዳጅነት  የኦሮሚያ ክልል ተጠቃሚ አንተ ብቻ  ለመሆን ትባጃለህ ። ” ይህ መንገድ የጥፋት መንገድ ነው ፡፡  ይኼ ያፈጠጠ የፓለቲካ በጎች የጭፍን አካሄድ ነው ! መሬት  ላይ ያለው ለዘውግ ፓለቲከኞች የሚመረው   እውነት ፣ አማራም ፣ ትግሬም ፣ ሲዳማም ፣ ሱማሌም ፣ አፋርም … ሁሉም ክልሎች  ያልፈጠሩት መሬት ባለቤት ነን ማለት አይችሉም ። እንደ አገር ልንቀጥል ከፈለገን ሰማዩ ላይ ያለችው  ፀሐይ የእኔ ናት ማለታችንን ማቆም አለብን ።እወቅ መሬት ከአሥሩ ፕሌኔቶች አንዷ ናት ። እንግዳ ሆኖ ለመጣው ሰው  መኖሪያ ሆናለች ፡፡  እንደ ፈጣሪ ፈቃድ ። …

ማርስ ላይ ሰው ሊኖር ይችላል ። ይላሉ ሣይንቲሥቶቹ ። ሊኖር ይችል ይሆናል ። ማን ያውቃል ።  ሰው በዩኒቨርሰ ውሥጥ ብቻውን አይደለም ።ቢያንሥ መሪዎች ይኽንን እውነት መረዳት አለባቸው ። ከበግ ፖለቲካል ኢኮኖሚ አንፃር ይኽ እውነት ለጥቅም ሲባል በግን ከመምራት ወደ እውነተኛ የበግ እረኝነት ያሸጋግራቸዋል  ።

ወዳጄ ይኽንን እውነት በጥልቀት ተገንዘብ ። ተረዳ ። በሴራ ፖለቲካ ተክነህ ፤  ” መንገድ መሪ ፤ አውራ ፖለቲካል  በግ  ” ከሆንክ ግን ያለጥያቄ የሚከተልህ በግ ብዙ ነው እና በታሪክ ተወቃሽ ሆነህ ህይወትህ እንዳያልፍ ተጠንቀቅ ። … ሞት አይቀርም ሥም አይቀበርምና !

1 Comment

  1. ከላይ የተዘበዘበዉን በባዶ የበላይነት እና የማንነት ቀዉስ በፈጠረዉ ስሜት በሚሰቃይ የሲቃ ድምፅ ዉስጥ ተሁኖ የተፃፈዉን አነበብኩ። ” ጅል አይሙት እንዲያጫዉት ::” የሚባለዉ እዚህ ላይ ነዉ። በበግ ፖለቲካ አገላለፅ ዉስጥ በመጀመሪያዉ መስመሮች አከባቢ ማሰብ የጀመረ ሰዉ አይነት ሐሳቦችን የያዘ ይመስል ነበር፤ ወደ መሐሉ እና መጨረሻ የአረፍተ ነገሩ መዳረሻ ላይ ሲደረስ ነዉ የፀሐፊዉ በበታችነት ስሜት ደዌ የተጠቃ መሆኑ የተገለጠዉ። ጅላንፎነቱን ያደመቀዉ ደግሞ ለክልል ያለዉ ትርጓሜ ነዉ። በፀሐፊዉ እዉር ድንብር አተያይ “ማንም የፈለገበት የአለም ሀገር ላይ ሂዶ የእራሱን መንግስት መስርቶ በሰላም መኖር ይችላል ማለት ነዉ።”

Leave a Reply

Your email address will not be published.