September 19, 2022
ጠገናው ጎሹ
ዘመን መለወጫም ተፈጥሯዊ ህግን ተከትሎ በራሱ የጊዜ ምህዋር ላይ በሚፈራረቅ ሂደት ውስጥ በአጠቃላይ የሰው ልጅን ወይም የተወሰነ ማህበረሰብ ሁለንተናዊ መስተጋብርና የእድገት ግስጋሴ አወንታዊ ወይም አሉታዊ መሆኑን ወይም አለመሆኑን ከሚነግሩን ዓመታዊ በዓላት አንዱ ነው። ሁሉም ነገር የሚከናወነው በጊዜ ሂደት ውስጥ ነውና ።
እድሜ ቁጥር ብቻ መቁጠር ሲሆን ብዙም ትርጉም እንደሌለው ሁሉ የዘመን መለወጫም በቁጥር ብቻ ተቀምሮ የሚቆጠርና የሚከብር ከሆነ ትርጉም አይኖረውም። ቆጠርነውም አልቆጠርነው የተፈጥሮ ህግ ምህዋሩን ጠብቆ ይጎዛልና ። የዘንድሮው የዘመን መለወጫ ከብዙ ዓመታት በፊትና በተለይም አምስተኛ ዓመቱን በያዘው የእነ አብይ አህመድ አገዛዝ ሥር ሆነን ከሳለፍናቸው የመከራና የውርደት የዘመን መለወጫ ዓመታት ሲሆን የተሻለ ካልሆነም ይበልጥ ያልባሰ እንዳይሆን ለማድረግ ሳንችል የመቅረታችን ውድቀት በእጅጉ ያማል። በዚህ እጅግ መሪር ሁኔታ ውስጥ እጓየጎጥንም ( በመኖርና ባለመኖር አረንቋ ውስጥ እየዳከርንም) እጅግ አብዛኛዎቹ የዘመን መለወጫ መልእክቶቻችን ከተለመደው የእንኳን አደረሰንና ድርጊት አልባ ምኞት መግለጫነት አላለፉም ። ስለ እውነት በእውነት ከተነጋገርን ይህ ውድቀት የሸፍጠኛ፣ ሴረኛና ጨካኝ የፖለቲካ ቁማርተኞችና ግብረ በላዎቻቸው ሥርዓተ ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ፍፃሜ የሚያገኝበትን የነፃነትና የፍትህ መንገድ በመሳታችን ምክንያት የተፈጠረ ነው። ለዚህም ነው የዘንድሮው የዘመን መለወጫ የእንኳን አደረሰንና የመልካም ምኞት መልእክቶቻችን ብዙም ስሜትን የማይስቡ የሆኑብን።
አዎ! አብዛኛዎቹ መልክቶቻችን ከብዙ ዓመታት ውድቀት ተምሮ ፣ የዛሬን መሪር ሃቅ በግልፅና በቀጥታ ተጋፍጦ መጭውን ጊዜ በባዶ ተስፋና ምኞት ሳይሆን በተግባራዊ አቋምና ቁመና እውነተኛ የለውጥ ዘመን አድርጎ ለመቀበል የሚያስችል የጋራ ተጋድሎ አስፈላጊነትን በግልፅ የሚያመለክት ይዘት የላቸውም። ከዚህ ይልቅ የጎሳ አጥንት ስሌት ፖለቲካ ቁማርተኞች (የኢህአዴጋዊያን/ብልፅግናዊያን) የፖለቲካ ሥርዓት ባስከተለው መከራና ውርደት ምክንያት የቀን ተቀን ህይወቱ የተመሰቃቀለበት አገሬ ሰው የዘወትር ጥያቄና ምኞት የሆኑትን ሰላምን፣ እርቅን ፣ ፍቅርን፣ ይቅርታን ፣ እምነትን፣ በጎ ራዕይን ፣ ተስፋን ፣ መከባበርን፣ አንድነትን፣ ደግነትን፣ ወዘተ መላልሰው የሚሰብኩ ሆነው ነው ያገኘኋቸው ። ፈተናው ያለው ቃልና ተግባርን በማዋሃድ እውነተኛ ፍስሃ የሚገለፅበትን ሥርዓትና ዘመን እውን ከማድረጉ ላይ እንጅ ከባዶ ስብከትና ዲስኩር እንዳልሆነና እንደማይሆን አልቃሽና ዘፋኝ ሆነን የዘለቅንባቸው ሦስት ዓሥርተ ዓመታት ትምህርት በተገባ ነበር። አለመሆኑ ያሳዝናል።
መቼም የጊዜ መፈራረቅ ከተፈጥሮ ህግጋት አንዱ ነውና ከክርስቶስ ልደት ጀምሮ ዓመተ ምህራት በሚል የምንጠራውን የዘመን አቆጣጠር ሁለት ሽ አሥራ አራተኛውን አልፈን ወደ ሁለት ሽ አሥራ አምስተኛው (እ.ኢ የዘመን አቆጣጠር ቀመር) ከገባን አንድ ሳምንት ሆነን።
ይህንኑ ዘመን መለወጫ አስመልክቶ (ከ2014 ወደ 2015) ከገዥዎች ፣ ከሃይማኖት መሪዎች እና ከሌሎች ወገኖችም የተላለፉትን መልእክቶች በጥሞና አንብቢያለሁ ፣ አድምጫለሁም ።
የመከራና የውርደት አገዛዛቸውን እንደ ምድራዊ የሰላምና የእድገት ጎዳና እና የፅድቅ መንገድ አድርገው ለዘመናት ሲያደነቁሩን ስለ ኖሩትና አሁንም እያደነቆሩን ለመቀጠል ስለ ወሰኑት እኩያን ገዥ ቡድኖች ከቃላት ይልቅ ተግባራቸው ስለሚናገር ብዙ ማለት አያስፈልገኝምና ለማሳያነት ያህል ብቻ የሚከተለውን ልበል።
ለዘመናት ባሰለጠኑት ሸፍጠኛ አንደበታቸው መከረኛውን ህዝብ በማታለልና የግልብ ስሜት ፖለቲካ ሰለባ በማድረግ የቤተ መንግሥቱን ሥልጣነ መንበር በተረኝነት ከተቆጣጠሩ ብዙም ሳይቆዩ የግፍ ግድያ ሰለባ ለሆኑ ብዙ ሽዎች እና የቁም ሰቆቃ ሰላባ ላደረጓቸው ብዙ ሚሊዮኖች እንኳንስ ብሔራዊ ሃዘን ሊያውጁ አገር እመራለሁ እንደሚል ፖለቲከኛ እናዝናለን ለማለት የሞራል አቅም የሌላቸው ገዥ ቡድኖች “እንኳን ከድል ጋር አደረሰን” ሲሉን ጨርሶ ህሊናቸውን አልጎረበጣቸውም። ለነገሩ ህሊናውን የሚጎረብጠው ሰው የሚያሰኝ ህሊና ያለው ሰውና የሚገርም አይደለም።
“የምናስረውና ከእሥር የምንፈታው የማንንም ትእዛዝ ሳይሆን የፈጣሪን ትእዛዝ እየተቀበልን ነው” በሚል ፈጣሪን ሳይቀር የግፍና የሸፍጥ ፖለቲካቸው ተባባሪ የሚያደርጉ የቤተ መንግሥት ፖለቲከኞች በየትኛው የሞራል ልዕልና የድል ዘመን አብሳሪ ሊሆኑ እንደሚችሉ እንኳን ለመቀበል ለመገመትም ያስቸግራል።
የሸፍጥና የሴራ ፖለቲካ ቁማርተኞች ለዘመናት የመጣንበትንና አሁንም በአዛኝ ሁኔታ ተዘፍቀን የምንገኝበትን መሪር እውነታ ወደ ታች ዘቅዝቀው እያስነበቡ ሊያሳምኑን ሲሞክሩ ከነውርነትም አልፎ ወንጀል ነውና በቃችሁ እስካልተባሉ ድረስ ከዚህም የከፉ የሸፍጥና የስላቅ “እንኳን አደረሳችሁ” ዓመታትን ሊያስቆጥሩን እንደሚችሉ የሚያጠራጥር አይደለም ።
የዘመን መለወጫ መልእክቶቻችን ከባዱ ፈተና አጠቃላይ እውነትን (general truth) ለዘመናት ወደ መጣንበትና አሁንም እጅግ አስከፊ በሆነ ሁኔታ ወደ ምንገኝበት መሪር እውነታ አውርዶ ለማየትና እውነተኛ ሰላም፣ ፍትህ፣ ፍቅር ፣መተሳሰብ እና የጋራ እድገት የሚረጋገጥበትን ሥርዓት እውን ለማድረግ የሚደረገውን ትግል የሚመጡ ካለመሆናቸው ላይ ነው።
የእንዲህ አይነት የዘመን መለወጫ መልእቶች የይዘትና የጥልቀት ጉድለት የታየው በፖለቲካው አውድ ብቻ ሳይሆን በሃይመኖት ተቋማት ጭመር ነው ።
ባህላችን የሃይማኖት መሪዎችንና አስተማሪዎችን ለማሄስ (ለመተቸት) ጨርሶ ትእግሥት የሌለው መሆኑን እገነዘባለሁ። እውተኛው ፈጣሪ ግን እንዲህ አይኑቱን የማይጠቅም የአስተሳሰብ ባህል ተቀብሎ በትችት ሰንዛሪዎች ላይ ይፈርዳል የሚል እምነት የለኝም። ኋጢአት ወይም ስህተት የሚሆነው የትችት መነሻችን ሊስተካከል ይገባዋል የምንለውን የአስተሳሰብና የድርጊት ስሀተት በተገቢው መንገድ ሳይሆን በግል ህይወት አኗኗር፣ በግል ህይወት አስተሳሰብና በሚጠሩበት የመሪነት ማእረግ ላይ ሲያተኩር ነው ። ማህበረሰብን ወይም አገርን በተመለከተ በተፈጠረና ሊፈጠር በሚችል ጉዳይ ዙሪያ እስካተኮርን ድረስ እና ይህንኑ በአግባቡ ለማቅረብ እስከቻልን ድረስ ሌላው መመዘኛ ብዙም ሚዛን የሚደፋ አይሆንም። አስተያየቴም በዚሁ መሠረታዊ መርህ ላይ የተመሠረተ ነው ።
በተለይ እርቅን፣ ይቅርታንና ሰላምን ሁሉን አቀፍ ከሆነ የሽግግር ጊዜ ፍትህ ውጭ በማድረግ በጎሳ ማንነት የግፍ ግድያ እና በሥልጣን ሽኩቻ ጦርነት ምክንያት በፈሰሰው የንፁሃን ደምእ ጆቻቸው የተዘፈቁ ሁለት የአንደ ሥርዓት አንጃዎች (የህወሃትና የብልፅግና) ጉዳይ ብቻ አድርጎ የመውሰድ እስተሳሰብና አካሄድ በእጅጉ የተንሸዋረረና አደገኛ በመሆኑ በፍጥነት ሊታረም (ሊስተካከል) ይገበዋል።
በግፈኛና ዘራፊ ገዥዎች በእጅጉ የበሰበሰውንና የከረፋውን የፖለቲካ ሥርዓት የግለሰቦችን ወይም የተወሰኑ ቡድኖችን አለመግባባት ለመፍታት በምንሞክርበት እጅግ የተድበሰበሰ የአንተም ተው የአንተም ተው ባህላዊ መንገድ ለመፍታት መሞከር ውጤቱ በነበሩበት ብቻ ሳይሆን እጅግ በባሰ የቀውስ አዙሪት ውስጥ ተመልሶ መዘፈቅ ነው የሚሆነው።
እየሰማናቸው ያሉ አብዛኛዎቹ መልእከቶች ወደ ፊት መንጎዱን የማያቋርጠውን ተፈጥሮዋዊ የጊዜ አቆጣጠር ህግ ከመቁጠር አልፈው ወደ መሬት በመውረድ ዘላቂ የመፍትሄ ሃሳብን የመውለድና አበልፅጎ ሥራ ላይ የማዋል ይዘትና አቅም የላቸውም።
የራዕይ ግልፅነት ፣ የፅዕኑ ዓላማና መርህ ባለቤትነት ፣ የአስተሰሰብ ብስለት ፣ የአደረጃጀት ጥንካሬ ፣ የፖሊሲና ፕሮግራም ጥራት ፣ የአፈፃፀም ስልት ጥራት እና የተቀናጀ አሠራር መኖር ፈታኝ ሁኔታዎችን (challenges) ወደ መልካም አጋጣሚነት ለመለወጥ ያስችላሉ። እነዚህ ሁኔታዎች የሌሉበት ሁለተኛው እጣ ፈንታ በፈታኝ ሁኔታዎች የበለጠ ደካማ ከመሆን አልፎ የውድቀት አዙሪት ሰለባ መሆንን ያስከትላል። እስካሁን በአገራችን እየሆነ ያለው ሁለተኛው እጣ ፈንታ ነው ። ለዚህ ነው ለዘመናት የዘለቁትን ፈታኝ ሁኔታዎች ወደ መልካም እድልነት ለመለወጥ የሚያስችል አመርቂ ሥራ ባልሠራንበት መሪር እውነታ ውስጥ ሆነን አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር “ኢትዮጵያ ብዙጊዜ ተፈትና ፈተናውን ተወጥታለችና አሁንም ትወጠዋለች“ የሚለው መፈክር አሁን ላለንበት እጅግ አስከፊ ሁኔታ አልሠራም ያለን።
እናም ልብ ያለው ልብ ይበል!