አንድ አፍታ ከኢትዮጵያውያን ወታደሮች ጋር በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል… በዲ/ን ተረፈ ወርቁ

‘‘… ሀገርህን ጠላት እንዳይደፍራት ወታደር ሆነህ ጠብቃት፣ እንደ አባቶችህ ጀግና ሆነህ አሳያት፣ በጀግንነት ታሪክ ሥራላት፣ ታሪክ ያለው ከወታደርነት ነው፣ ጀግንነት ያለው ከወታደርነት ነው፣ ጀብዱ ያለው ከወታደርነት ነው፣ ታላቅ ስም ያለው ከወታደርነት ነው፡፡’’ የሚል የአባቶቻችን የጀግንነት የአደራ ቃል ውርስ አለን እኛ ኢትዮጵያውያን፡፡

በርግጥም ደግሞ ታሪካችንን ስንፈትሽም- ታላቁ የዐድዋ ድል የአርበኝነት፣ የወታደርነት ውጤት ነው፣ የአምስት ዓመቱ የጣልያን ወረራና የኢትዮጵያዊያን ድል የወታደርነት ውጤት ነው፡፡ ካራማራ የወታደርነት ውጤት ነው፣ የኢትዮጵያ የተከበረ ታሪክ የወታደር ታሪክ ነው፡፡ ለምን ሲባል- ኢትዮጵያ የተከበረችው በጀግኖች ልጆቿ፣ በወታደሮች ክንድ ነውና!!

በዛሬ ጽሑፌ ጀግኖች ኢትዮጵውያን ወታደሮች በተመለከተ ለመጻፍ የተገደድኩት ከሰሞኑን ወንድሜን ለመጎብኘትና ለማስታመም በአምስቱ ዓመታት የኢጣሊያ የፋሽስት ወረራ ዘመን ሀገራቸውን ከጠላት ለመታደግ ኢትዮጵያውያን የጦር መኮንኖች፣ ምሁራንና ጀግኖች ዐርበኞች ባቋቋሙት በጥቁር አንበሳ ጀግኖች መታሰቢያ ስም በተቋቋመው ጥቁር አንበሳ ሪፈራል ሆስፒታል እመላለስ ነበር፡፡ ታዲያ በቆይታዬ አንድ ረፋድ ማለዳ ላይ ከሰሜን ግንባር ቆስለው መጥተው በሆስፒታሉ የአጥንት ሕክምና ክፍል ሕክምናቸውን እየተከታተሉ ከሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወታደሮች ጋር ቆይታ አድርጌ ነበር፡፡

ሰብሰብ ብለው እያወጉ ፀሐይ እየሞቁ ከነበሩት ወታደሮች መካከል ሆኜ ስለ ውትድርና ሕይወታቸውና ስለ ሰሜን ጦር ግንባር ቆይታቸው ወግ/ጨዋታ ጀመርን፡፡ የቁስላቸውን፣ የሕመማቸውንና ያለፉበትን ክፉ ትዝታቸውን ለአፍታም ቢሆን ለመርሳት የቆረጠ በሚመስል ስሜት ከእኛ ዘንድ ፈንጠር ብለው የነበሩ ሦስት ወታደሮችም ተቀላቀሉን፡፡ ታዲያ በወጋችን መካከልም በዕድሜ ጠና ያለ ከአማራ ክልል የመጣ ቁስለኛ ወታደር ቁጭት፣ የሀገርና የወገን ፍቅር በሚነበብበት የስሜት ገጽታ ውስጥ ሆኖ፤

ወንድሜ አየህ ለሀገር መሞት ታላቅ ክብር ነው… ዛሬ አንተም፣ እኔም ሁላችንም የቆምንባት የኢትዮጵያ ምድር በቀደሙ ጀግኖች አባቶቻችንና እናቶቻችን ደምና አጥንት መሠረትነት የተገነባ ነው፡፡ ታሪክ እንደሚነግረን በኢትዮጵያ ጉዳይ ሁሉም አርበኛ፣ ሁሉም ጦረኛ ነው፡፡ ሁሉም ሰንደቁን አስቀድሞ ይገሠግሣል፡፡ ጀግኖች ኢትዮጵያውያን በየዘመናቱ ጀብዱ እየሠሩ ዛሬ ላይ ኮርተን የምንኖርባት ሀገር፣ ኮርተን የምንናገረው፣ በአሸናፊነት የምንመሰክረው ታሪክ አኑረውልናል፡፡ እኒያ ጀግኖች ታሪክ ሰርተው፣ ስማቸውን ከመቃብር በላይ ትተው ‘‘ሀገሩን ያስደፈረ ታሪክ ይውቀሰው፣ ዐፅማችንም እሾኽ ሆኖ ይውጋው!” ብለው ቃል ኪዳን አስረው፣ አደራ ሰጥተው አልፈዋል… ሕ-ሕ-ም-ም የቅስሉ ሕመም መጣ ሄድ እያለበት ያለው ወታደር በረጅሙ ተንፍሶ ለጥቂት ሰከንዶች ዝም አለ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በጦርነቱ ማን ድል አደረገ?  በቀጣዩ የወያኔ ዳግም ወረራስ ማን ድል ያደርጋል? ---ፊልጶስ

በዚህ ጀግና ወገኔ የአፍታ ዝምታ ውስጥ- የወታደር፣ የዐርበኛ ልጅ እንዲሁም የታሪክ መምህር እና ጋዜጠኛ ነኝና ከጉንደት እስከ ጉራዕ፣ ከዐድዋ እስከ ማይጨው፣ ከኦጋዴን እስከ ካራ ማራ… ያበበ የኢትዮጵያውያን ጀግንነትና እምቢ ለነጻነቴ ባይነት- የኢትዮጵያ ድንበር ሳይገድበው አውሮፓ ምድር- ሮም/ጣሊያን ድረስ ተሻግሮ ዓለምን ያስደመመ፣ ያስደነቀ መሆኑን ታሪካችንን እየፈተሽኩ ማስብ፣ ማሰላሰል ያዝኩ…፡፡

ጀግናው ወታደር ወደ ወጋችን መለስ አለና… ይኸውልህ ወንድምዓለም አለኝ ሙሉ ቀልቤን በሚፈልግ ዓይነት ስሜት በሚነበብበት ፊት… እኔ ቆስዬ እዚህ ሕክምናዬን በጥሩ እየተከታተልኩ ነው፤ ግና የእኔን ወደ አዲስ አበባ መምጣት ቤተሰቤም ሆነ ባለቤቴ አያውቁም፡፡ እንዳይደነግጡ ብዬ አልነገርኳቸውም፡፡ ስልክ በደወሉ ቁጥር ሲያገኙኝ – ምነው አለወትሮ ስልክ ደጋግሞ ሠራ ሲሉኝ… ‘‘አይ አይደለም ስንቅና ትጥቅ ለማደራጀት ሰሞኑን ከተማ ስለገባሁ ነው፤’’ ብዬ እያልኳቸው ነው፡፡ ሕክምናዬን ከጨርስኩ በኋላ ግን ቤተሰቤን አይቼ ጦርነቱ ካልተቋጨ ወደ ግዳጅ እመለስ ይሆናል፡፡

ህ…ህ… ብቻ ወንድምዓለም በርግጥም ጦርነት ከባድ፣ አስከፊ ነገር ነው… መከራው፣ ሰቀቀኑ ብዙ ነው፤ የጦር ሜዳ ጓድህ ፊት ለፊትህ ተመትቶ ወድቆ ስታይ፣ በደም የተነከረ የወገንህን ሬሳ እየተራመድክ ወደ ፊት ስትጓዝ ጥልቅ ኀዘን ውስጥ ትገባለህ፡፡ መለስ ብለህ የሀገርና የሕዝብህ አደራ ትዝ ሲልህ ደግሞ ነፍስህ ትቃትታለች… እንዲህ እንደ አሁኑ ጦርነቱ ከራስህ ወገን ጋር መሆኑ ትዝ ሲልህ ደግሞ ግራ ያጋባኻል፤ ብቻ ፈጣሪ በቃ ይበለን!

ከእኛ ፈንጠር ብሎ በተሽከርካሪ ወንበር/በዊልቼር ላይ የተቀመጠ ወጣት ቁስለኛ ወታደር ቁጣና ቁጭት በተቀላቀለበት ድምፀት እ…እ… ማነው ወገን?! እነርሱማ ወገን ሊሆኑ አይችሉም… በእጁ የተቀመጠበትን የዊልቸር እጀታ እየመታ ሕ-ሕ-ም-ም እነርሱ ወ-ገ-ን… ልዳን እንጂ አሁንም የኢትዮጵያን ጠላቶች ለማጥፋት ወደ ጦር ግንባር እመለሳለኹ…፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ባንዲራው የ ‘ሁላችንም’ ነው!! – ታሪኩ አባዳማ

ቁጣና እልህ ያየዘው ወጣቱ ወታደር፤ ‘‘ኸውልህ ወንድም እኔ ከኬንያ ጠረፈ ከጂንካ ነው የመጣሁት፤ ጂንካ የሚባል ሀገር ታውቃለህ አለኝ፤’’ አዎ እንዴ! ስለጂንካንማ በደንብ አውቃለኹ አልኩት፤ ማወቄን ለማስረገጥ ያህልም ስለአካባቢው የማውቀውን አንዳንድ ነገሮች አነሳኹለት፡፡ የጂንካው ወጣት መልካም- ይኸውልህ እኔ በመጀመሪያ የዛሬ ዓመት በተሳተፍኩበት የጦር ግንባር ቀላል ጉዳት ገጥሞኝ ባሕር ዳር ታከሜ ወደ ወገን ጦር ተቀላቅዬ ነበር፡፡ ከወር በፊት ግን በተሳተፍኩበት ጦርነት እግሬን በዲሽቃ ተመትቼ ነው እዚህ ለከፍተኛ ሕክምና የመጣሁት አለኝ በፋሻ ወደተጠቀለለው የእግሩ ቁስል ዝቅ ብሎ እያሳየኝ፡፡

ሌላኛው ከእርሱ አጠገብ የተቀመጠ ወታደር ቁስሉን እያየ፤ ‘‘ወንድሜ እንደው የበረደው ጥይት አጋጥሞህ እንጂ ዲሽቃማ መጥፎ አይደል፣ ገንጥሎ አይደለ እንዴ የሚጥልህ?!’’ አለው… ወጣቱ ወታደርም፤ ‘‘የምሽጋችንን ካብ ድንጋይ አልፎ የመጣ የዲሽቃ ጥይት ነው ያገኘኝ እንጂ እንዳልከው ጥይቱ ሳይበርድ አግኝቶኝ ቢሆኖ ኖሮ ጉዳቴ የከፋ ይሆን ነበር፡፡’’ አለው በመጽናናት ስሜት ውስጥ ሆኖ… ወጋችን ቀጥሏል…፡፡

በሰሜኑ ግንባር ሁለት ዓመት ሊደፍን የቀናት ዕድሜ ብቻ በቀረው ጦርነት ከተሳተፉት ወታደሮች ጋር ያወጋነውን በዚህ ገጽ ላይ ሁሉንም ለማንሳት፣ ለመጻፍ ግን የእነዚህ ወገኖቻችን፣ የወታደሮቻችን ክብር፣ የሀገር ምሥጢር… የሚባል ልጓም አለና በዚህ ልቋጨው… ግና ሀገራችን ኢትዮጵያ ከጦርነት ወጥታ – ለሕዝቦቿ፣ ለአፍሪካውያንና ለመላው ጥቁር ሕዝቦች የነጻነት የሰላምና አንድነት ዓርማ ሆና ዳግም ትታይ ዘንድ የሰላም ፈላጊ ኢትዮጵያውያን ምኞታችን ይሳካ ዘንድ በመመኘት፤

የዛሬውን ጽሑፌን ብርጋዴር ጄኔራል ዋሲሁን ንጋቱ ከአራት ዓመት በፊት፤ ‘‘ያልታደለች ሀገር፣ ሕዝብ እና ሰራዊት’’ በሚል አርእስት ባበረከቱልን መጽሐፋቸው ውስጥ ባሰፈሩት፣ የሥራ ባልደረባቸውና ጦር ጓዳቸው በሆኑት በሜጀር ጄኔራል ሁሴን አህመድ ጠቃሚ ምክር ለመደምደም ወደድኩ፣

ተጨማሪ ያንብቡ:  የጭንቀላት ሥጋ መብሰሉ ለማይቀረው እንጨት ይፈጃል - ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

‘‘ሕይወት ብዙ ውጣ ውረድ አላት፡፡ ክፉም በጎም ይፈራረቁብናል፡፡ ተቃራኒ ስሜቶች ይቀራመቱናል፡፡ የእኔም ሕይወት እንደብዙዎቹ የጦር ጓዶች ሁሉ ጉዞዬ በሬትና በማር የተሞላና የተለወሰ ነው፡፡ አብዛኛው የሬት ጉዞ እኛው ሰዎች የፈጠርነው ነው፡፡ ሰው ከእንሰሳት ሁሉ የላቀ ነው ይባላል፡፡ እውነትም የሚሠራው የሳይንስና የቴክኖሎጂ እመርታ ተኣምር የሚያሰኝ ነው፣ የፍቅር ስሜቱም እጅግ የመጠቀ ነው፡፡

ነገር ግን አለመግባባቱን በጥበብና በትዕግሥት፣ በውይይትና ቀርቦ በመነጋገር በሰላማዊ መንገድ መፍታት እየተሳነው በተለያዩ ሰበቦች ሁከት እያነሳ የጥበብና የፍቅር ውጤቶችንና ስሜቶችን የሚያውድም ግጭት እየፈጠረ እንደተራበ ተኩላ እየተነካከሰ ራሱንና አካባቢውን በጦርነት ያወድማል፡፡ ለዚህም እኛ የዓይን ምስክሮች ነን፡፡

ኢትዮጵያ ሀገራችን የተፈጥሮ ሀብትና ውበት ሳታጣ ለዘመናት የጦርነትና ጉስቁልና (የድህነት) መድረክ ሆና አየናት፡፡ ምነው ቢበቃ!! ምነው በሆድ ሳሆን በጭንቅላት እያሰብን ሰላምንና ፍቅርን ብንላበስ?! ምነው ለምንወልዳቸው ልጆች ሰላምን ፍቅርን ዕድገትን ብናወርሳቸው?! እየወለድን ለጦርነትና ለድህነት! ማር ማውረስ ተስኖን ሬት የምናወርሳቸው ከሆነ መውለድን እናቁም!!

ሰላም ለኢትዮጵያ! ሰላም ለምድራችን!

Leave a Reply

Your email address will not be published.