ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ያቀረቡትን ሪፖርት አስመልክቶ
_______
ንቅናቄያችን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አበቤ ዛሬ መጋቢት 5 ቀን 2015 ዓ.ም ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት «ከአንዳንድ ክልሎች የሚደረገው ከፍተኛ ፍልሰት መንግስትን በመጣል በኃይል ስልጣን ለመቆጣጠር ያለመ ነው» ሲሉ ሪፖርት ማቅረባቸውን ከተለያዩ ሚዲያ ዘገባዎች እና ከውስጥ ምንጮቻችን አረጋግጧል፡፡
.
ከንቲባዋ በሪፖርታቸው ይህን መሰል አደገኛ ከፋፋይ እና የዘር ማጥፋት ወንጀል ቅስቀሳ ማድረጋቸው አገረ መንግስቱን አደጋ ላይ የሚጥል እና በማናቸውም መመዘኛ ተቀባይነት የሌለው የዓለም አቀፍ ወንጀል ጥሪ ነው፡፡ ዜጎች በነፃነት ተዘዋውረው የመስራት እና የመኖር ሰብዓዊ መብት ያላቸው መሆኑ ኢትዮጵያ በፈረመቻቸው ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ሥምምነቶች ድንጋጌዎች እና በሥራ ላይ ባለው ሕገ-መንግስት ጭምር የተረጋገጡ ተፈጥሯዊ መብቶች ናቸው፡፡
.
ይሁን እንጂ ከንቲባዋ «የኦሮሚያ ሚዲያ ኔትዎርክ» እየተባለ በሚጠራው ጽንፈኛ እና በአንድ ወቅት መንግስት ራሱ «የሽብርተኞች መጠቀሚያ ነው» ብሎ በፈረጀው ሚዲያ በተከታታይ የወጡ ቅስቀሳዎች ቅጥያ የሆነ አደገኛ የወንጀል ቅስቀሳ አድርገዋል፡፡ ዓለም አቀፍ ከተማን በከንቲባነት እመራለሁ ከሚል የመንግስት ባለስልጣን እንዲህ ዓይነት አደገኛ ቅስቀሳ በሪፖርትነት መሰማቱ እስካሁን ሲፈፀሙ ለነበሩ በሰብዓዊነት ላይ የተፈፀሙ ወንጀሎች እና እየታወጀ ላለው የዘር ማጥፋት ወንጀል ከለላ የሚሆን አሳፋሪ የወንጀል ድርጊት ጥሪ ነው፡፡
.
በመሆኑም ሁሉም አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን እና የዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡ ይኼንን አደገኛ የዘር ማጥፋት ወንጀል ቅስቀሳ ትኩረት በመስጠት አስቀድሞ ተገቢውን እርምጃ እንዲወስዱ ታሪካዊ ጥሪ እያደረግን፤ በተለይ የዓለም አቀፉ ማኅበረሰቡ ይኼንን ባያደርግ በሩዋንዳ የፈፀመውን ታሪካዊ ስህተት የሚደግመው መሆኑን ማስረገጥ እንሻለን፡፡
.
በሌላ በኩል የፌደራል መንግስቱም ሆነ ገዥው የብልጽግና ፓርቲ ይኼንን አደገኛ የዘር ማጥፋት ወንጀል ቅስቀሳ ያደረጉትን ግለሰብ ከስልጣን እንዲያነሳ እና ለፍርድ እንዲያቀርብ ጥሪ እያቀረብን፥ መሰል ድርጊት በድጋሚ እንዳይፈፀም መንግስታዊ ማረጋገጫ ጭምር እንዲሰጥ ጥሪ እናቀርባለን፡፡
.
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ(አብን)
አዲስ አበባ፥ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ
መጋቢት 5 ቀን 2015 ዓ.ም.
ተጨማሪ ያንብቡ:  ከመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የተሠጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

Leave a Reply

Your email address will not be published.