የአዲስ አበባ ባለቤት ማነው? (ስለአዲስ አበባ ባለቤትነት በምሥጢር የቀረበ ሰነድ) – ኀይሌ ላሬቦ

adancech 77

Who Owns Addis Ababa – Finfinne Written By Dr. Abiy Legal Counsel

በቅርቡ የአዲስ አበባ ከንቲባ፣ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ከመናገሻ ከተማዪቷ ሸንጎ አባል የተነሡትን ጥያቄዎች ስትመልስ ስለአዲስ አበባ ሁናቴና የኦሮሚያ ክልል በከተማዪቱ ላይ ያለው መብት የተናገረችው፣ የሰሞኑ መነጋገርያ ሁኖ ሰንብቷል። ወይዜሯ እያስተጋባች ያለችው አዲስ ነገር አለመሆኑን አንባቢ እንዲገነዘበውና እንዲወያይበት የሚቀጥለውን የአገሩ ጠቅላይ መሪ፣ ማለትም የሊቅ ዐቢይ አሕመድ ከፍተኛ የሕግ አማካሪ በኢ. አ. በመጋቢት ወር በ2011 ዓ. ም. ላይ በምስጢር በጽሑፍ ያቀረበውን ምክንያታዊ ነጥቦች እዚህ ለጥፋለሁ። አማካሪው ስለባለቤትነቱ ጉዳይ የተለያዩ መላምቶቹን ካቀረበ በኋላ፣ “ወደድነውም ጠላነው፣ አዲስ አበባ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማ ናት። የክልሉ ሥልጣን ባለቤት ደግሞ የኦሮሞ ሕዝብና በሕጋዊነት በክልሉ የሚኖሩ የሌላ ብሔር ተወላጆች ነው፣ አራት ነጥብ፤” ሲል ይደመድማል።

“በሕጋዊነት በክልሉ የሚኖሩ የሌላ ብሔር ተወላጆች” የሚለው ንኡስ ዐረፍተ ነገር መሰመር አለበት ባይ ነኝ። አንድ “የሌላ ብሔር ተወላጅ” በአዲስ አበባ “ሕጋዊ ነዋሪ” ለመሆን ዋናው መስፈርቱ የክልሉን የሥራ ቋንቋ ማለትም ኦሮሞኛ ማወቅ የግዴታ እንደሆነ ከላይ አስቀምጦታል። አለበለዚያ ሕጋዊ ነዋሪ አይደለም ብቻ ሳይሆነ የዜግነት መብት ራሱ የሚኖረው ማለትም “በክልሉ መንግሥታዊ ሥራ ውስጥ ተመርጦ ወይንም ተመድቦ መሥራት፣ እንደማንኛውም የክልሉ ተወላጅ ሠርቶ መኖር፣ ከሥፍራ ሥፍራ መዘዋወር፣ ሀብትና ንብረት ማፍራትና መያዝ” የሚችለው ቋንቋውን እስካወቀ ድረስ ብቻ ነው። በአሁን ወቅት የዩኒቬርሲቲ ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ሥራ ማግኘት አቅቷቸው በቦዘኔነት የሚኖሩ የአዲስ አበቤዎች ዕጣ ፈንታ ምክንያቱ የኦሮሞኛ ቋንቋ አለማወቃቸው እንደሆነ ይኸ ሰነድ ግልጥ ያደርገዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የማንቸስተር ዩናይትድ አስገራሚ አቋም (ሻምፒዮን ሆነ)

ከዚህ አስተሳሰብ ጋር በማያያዝ ገፋ ብለን ብንሄድ ደግሞ፣ አሁን በኦሮሚያ ክልል እየተፈጸመ ያለው “የሌላ ብሔር ተወላጆች” ሀብትና ንብረት ማውደምና እንደዘር ማጥፋት ወንጀል መታየት ያለበት ጭፍጨፋ ከዚህ አስተሳሰብና የፖለቲካ መርህ የመነጨ መሆኑ የሚካድ አይመስለኝም። ስለዚህ “ጆሮ ያለው ይስማ”። ይኸንን አሬመናዊና አውሬአዊ ሁኖ መታየት የሚገባውን ሥርዐት ይዞ አገር ይገነባል የሚል ራሱን ከማታለል ውጭ ሌላ ፋይዳ አይኖረውም።

አማካሪው ጐሣዊ አመለካከቱን ለክርክሩ ተገቢ አድርጎ ለማቅረብ የሄደው ርቀት ታሪክን በመመርኰዝ ነው። ከዚህም የተነሣ፣ በሰነዱ መግቢያ ላይ ስለኢትዮጵያ ታሪክ የደሰኰረው አጭር የመክፈቻ ዲስኩር፣ አማካሪው፣ በጠቅላላ ስለታሪክና ታሪክ አጻጻፍ ሂደት፣ በተለይ ደግሞ ስለኢትዮጵያ ታሪክ ቅንጣት ታክል ዕውቀት እንደሌለው ያመለክታል። ይኸንን አስተያየቱን፣ “A FEW REMARKS ON ETHIOPIAN GOVERNMENT’S NEW HISTORY MODULE for HIGHER EDUCATION” በሚል  መጣጥፌ ላይ በአጭሩም ቢሆን ስለተቼሁት፣ የማንበብ ፍላጎት  ያለው ይኸንን  https://www.academia.edu/49427577 ማስፈንጠርያ በመጫን ሊመለከተው ይችላል።

ይኸንን የአገር ጠቅላይ መሪውን የሊቅ ዐቢይ ከፍተኛ ሕግ አማካሪን ጽሑፍ የተቋደስሁበት ዋናው ምክንያት፣ አሁን “ተረኞቹ” በመባል የታወቁትን፣ የኦሮሞ ጽንፈኞች ባለሥልጣናትን ጥራዘነጠቅነት ጥግ ለማሳየት እንጂ ሕገመንግሥቱ ስለአዲስ አበባ ባለቤትነት የሚናገረው አማካሪው እንደሚለው ነው ለማለት አይደለም። የአዲስ አበባ ባለቤትነት ጉዳይ ራሱን የቻለ ጽሑፍ ስለሚወጣው አሁን ልዳስሰው አልደፈርሁም፡፡ ምናልባት ጊዜ ሲገኝ ወደፊት በአጭሩም ቢሆን ሊነካ ይችል ይሆናል። ዋናው ዓላማዬ በመግቢያው ጽሑፌ እንዳመለከትሁት አማካሪው ስለኢትዮጵያ ታሪክ በመክፈቻው ያለው ከአንደኛ ክፍል ተማሪ እንኳን የሚጠበቅ እንዳልሆነ ሁሉ፣ በአማካሪነት የተሾመበት የሕገመንግሥቱ ዕውቀት ራሱ ከሱ በላይ ጥራዘ ነጠቅን እንድናደንቀው ያስከጅለናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጠቅላይ ሚኒስትሩ የጠላት ኃይል እጁን እንዲሰጥ ያቀረቡትን ጥሪ ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች እጃቸውን እየሰጡ ነው

ሕገመንግሥቱ አዲስ አበባ ተጠሪነትዋ ለፌዴራል መንግሥት የሆነች፣ በነዋሪዎቿ የምትተዳደር ራስገዝ ከተማ ናት ይላል እንጂ፣ “የኦሮሚያ ክልል መናገሻ ናት” የሚል አንድም ቦታ የለም። የኦሮሞ መናገሻ መሆኗ ተጽፎ የሚገኘው በሕግ አማካሪውና በኦሮሞ ጽንፈኞች ምኞትና ዕቅድ ብቻ ነው። ስለዚህ እየነገሩን ያሉት በሕገመንግሥቱ የተጻፈውን ሳይሆን እያለሙ ያሉትን ምኞታቸውን ወይንም እየሠሩበት ያለውን የነገ ዕቅዳቸውን ነው ማለት ይቻላል። በትምህርትቤቶች አለሕግ የኦሮሚያን ሰንደቅ ዓላማ መሰቀሉን፣ የክልሉም መዝሙር መዘመሩን የተቃወሙትን የአዲስ አቤቤዎችን ተግባር በ”ኦሮሞ ጠልነት” የተረጐመው ጠቅላይ ሚኒስቴሩ ሊቅ ዐቢይም የዚህ ሕልምና ምኞት አራማጅ አይደለም የሚሉ ቢኖሩም፣ ተቋዳሽ ግን አይደለም ለማለት ያስቸግራል። እጁ እንዳለበት በተለያየ አጋጣሚ አሳይቷል ማለት ይቻላል።

ከሁሉም በላይ እጅግ በጣም አድርጎ የገረመኝ ነገር ቢኖር ግን፣ የአዲስ አበባ ሸንጎ ወይንም ምክር ቤት ተብዬው ነው። ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በልጅነቷ የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ሰንደቅ ዓላማ እንደክት ልብሷ ለብሳ ሽር ጉድ ትል የነበረችና በድርጅቱ የአስተሳሰብ እንቶፍንቶ እየታጠበች በከፍተኛ እንክብካቤ ያደገች መሆኗ መረሳት የለበትም። ስለዚህ አፍቃሪዎቿን አሳዳጊዎቿን ትታ፣ በሕጉ እንደሚጠበቀው ስለአዲስ አቤቤዎች ጥቅምና ፍላጎት ትቆማለች ማለት ከንቱ የሕልም እንጀራ ከመሆን አያልፍም። ይኸንን ለማድረግ ኅሊና የሚባል ብርቅ የሆነ ስጦታ ይጠይቃል። ጽንፈኞች ለዚህ ጸጋ አልታደሉም። ይሁንና ከሸንጎው/ምክርቤቱ አባል ለተጠየቀችው ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ እንደመስጠት ያንን ሁሉ ቅራቅንቦ ስለአዲስ አበባ ስታፈትት፣ አንድም የሸንጎው አባል ተቃውሞ አለማሰማቱ፣ የከተማዋ ምክር ቤት ከብሔራዊ የሕዝብ ምክርቤት በምንም እንደማይሻል አስገነዘበኝ። የነቁ የበቁና ለመረጣቸው ሕዝብ ታማኝ የሆኑ እንደራሴዎቹ ያሉበት ቤት ነው ሲባል ሰምቼ እሴየው ብዬ ነበር። ይኸ ሁናቴ ጥርት አድርጎ የገለጠልኝ ነገር ቢኖር ምክርቤት ተብዬው ያው የአደግዳጊና የነኁላላ ስብስብ እንጂ የሕዝብ አፍና ወኪል አለመሆኑን ነው። እጅግ በጣም ያሳዝናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አማራው በዘሩና በማንነቱ እየተገደለ ያለው በአብይ አህመድ እና በሽመለስ አብዲሳ ቀትተኛ ትዛዝ ነው

በተቀረ መልካም ንባብ።

Leave a Reply

Your email address will not be published.