ከሁለቱም ወገን በጦርነቱ ሰበብ ለሞቱት ከ600 ሺ በላይ ዜጎች አካላቸው ለጎደለ ተጠያቂው ማነው? – ሴና ዘ ሙሴ

 የፐሮ መስፍንን ሃሰብ የጽሑፌ  መግብያ አድርጌለሁ ።

″ ያንጊዜም ሆነ ዛሬ ፣ በበኩሌ  የጎሣ መነፅር የለኝም ። ልሳሳት እችላለሁ ። አሥተያየቴ ለአንዳንድ ሰዎች አይጥምም ። … ይሆናል ። ነገር ግን እግዚአብሔር ይመሥገን የጎሣ ምንም ነገር በውስጤ የለም ። ለእኔ በጎሣ ደረጃ ወርዶ ማሠብ ከሰውነት ደረጃ መውጣትና ወደአዘቅት መውረድ ነው ። እዚያ ተርታ በአካልም፣ በአስተሳሰብም በስሜትም አልገኝም ።

( ” አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ ” ገፅ 27 ፤ የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም መፅሐፍ ) “ሦሥት  ነገሮች አሉ ። እነዚህም ፦ የሁላችንም ኢትዮጵያ ፤ በተለያዩ ዘመኖች በኢትዮጵያ ውሥጥ የነበረው ሥርዓት ፤ በተለያዩ ዘመናት ሥርዓቱን የሚያንቀሳቅሱት ሰዎች ናቸው ። የመክሸፉ ሰንኮፍ ያለው እነዚህ ሦሥት የተለያዩ ነገርች ለይቶ ማየት ያለመቻል ላይ ነው ። አንዳንደ ሰዎች ይኼንን ሁሉ ከነጉድለቱ ለመወረስ አይፈልጉም ። መፍትሄው ነፃነት ነው ብለው በቅዠት ይነቃሉ ። ቅዠት  የምለው ለማዋረድ አይደለም ። እውነቱን ለመግለፅ ነው ። ማስረጃ የሚፈልግ ለአንድ  ሠዓት ያህል ብቻ ኤርትራና ሱማሊያ ያሉበትን ሁኔታ  ያጥና ። በሁለቱም አገሮች ያለው ሁኔታ በሽታው ያው በሥርዓቱ ላይ መሆኑንን ለመገንዘብ አያዳግተውም ። ህዝብን ሁሉ በነፃነት ፣ በእኩልነት ፣ የሚያቅፍ ህጋዊ ሥርዓት ከሌለ መበታተኑ የማይቀር ይሆናል ። መበታተኑም ቢሆን አይቆምም ።

ግን ማነው ነፃ የሚያወጣው ? ከማንስ ነው ነፃ የሚወጣው ? የወያኔ ፕሮግራም ኢትዮጵያን አማራ አድርጎ ሌላው ሁሉ ከአማራ ነፃ እንዲወጣ ነው ። ተገነዘቡትም ፣ አልተገዘቡትም የኢትዮጵያ ታሪክ ሁሉ አማራ  ለሚሉት አስረክበው ባዶ እጃቸውን ነፃ ሊወጡ ነው !? ግን አሥቸጋሪ ነው ። ኢሣያስ አፈወርቂ የሆነለት በመንግስት ደረጃ የኢትዮጵያን የቀን አቆጣጠር በፈረንጆች መለወጥ ብቻ ነው ። ዛሬም ኢትዮጵያዊነት በኤርትራ ውስጥ ጎልቶና ደምቆ ይታያል ። ራሱ ኢሣያሥም ቢሆን ኢትዮጵያዊነቱን በውስጡ ቀብሮ ይዞል ። ይኽ እኔ ራሴ ያረጋገጥኩት ነው ።

ገፅ 34 እና 35  ፤ ” አዳፍኔ ፍርሃትና መክሸፍ ” የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም መፅሐፍ )

 

አዳፍኔ እና መክሸፍ ለአለፉት 50 ዓመታት የኢትዮጵያ ህዝብ  የተጎዙበት መንገድ በአያሌ አበሳና ስቃይ እንዲሁም እጅግ በበዙ  እንቅፋቶች ፣ ወጥመዶች ፣ ጋሬጣዎች ፣ እሾኮች ፣ ጉድጎዶች ፣ አደናቃፊ ዲንጋዮች ፣ በአጠቃላይ በአዳፍኔ እና በመክሸፍ ለምን ተሟላ ?

በአዳፍኔ እና በመክሸፍ  የተሞላው በህዝብ ሥም ወደ ሥልጣን የሚመጡት ፣ በሥልጣን መገልገልን እንጂ ማገልገልን የማይፈልጉ ፣ እንደቀደሙት ጨቋኞች እነሱም በህዝብ ሥም ፤ በሤራ በተሞላ አገዛዝ ያውም  መርጠው በመጨቆን የአገዛዝ ዕድሜያቸውን ለማራዘም የሚጥሩ ሆነው በመገኘታቸው ነው ።

ዛሬና አሁን በኢትዮጵያ  የፖለቲካ  መንገድ ላይ በህዝብ ሥም ፣ ሥልጣን ይዘው ፣ ሠልፉን የሚመሩት ከመሳፍንት ዘመን ፖለቲካ ያልተላቀቁ ፣ ነፃ የህነውን ዜጋ ፣ “ በባርነት ውሥጥ ነህ ። “ ብለው የሚሰብኩ ።  በጠብመንጃ  ኃይል ፣ በተጭበረበረ ፍትህ ና እሥር እውነትን እሥካዳፈንክ  … ህዝባዊ ተቃውሞን በማክሸፍ ፣  ሥልጣኔን አይደፈሬ እሥካደረክልኝ  ጊዜ ድረስ ድሎትና ምቾትህን አላጎድልብህም ። “ ባዮች ናቸው ። ይኽ ድለላ ግን እሥከመቼ “ ደምቆ ና አሸብርቆ “ እንደሚቀጥል እግዜር ነው የሚያውቀው ። “ ዘርፈህ ሀብታም ሁን “ የሚሉ ።  ከወረዳ ጀምሮ  በሞዳሞድ ሥልጣን የያዙ ፤ በአገሪቱ ነገሰው ፤ ነገ  ሥልጣናቸውን  ለልጆቻቸው አውርሰው  ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ በፍትህ እና በዴሞክራሲ እጦት እያሰቃዩ ይቀጥላሉ ወይሥ ? ፈጣሪ ከወዲሁ “ በቃችሁ ! “ ይላቸዋል ? …

ዛሬ በኢትዮጵያ ፣ “ የተሥተካከለ ፣ ከህግ በታች የሆነ ፣ ለህግ የሚገዛ ፣ ህግን የሚያከብርና የሚያሥከብር  ፣ ህግ አሥፈፃሚ የለም ። “ ብሎ ለመናገር  የማያሥደፍሩ የህግ ጥሰቶች አጅግ በዝተው ፣ ህዝብን እያሥመረሩ  ነው ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዜጎች ከፍትህ ምንጭ ጠጥተው ይረኩ ዘንድ - ገለታው ዘለቀ

በጎበዝ አለቃ የምንመራ  እስኪመስል የህግ የበላይነት ተደምስሶ ፣ ግብዝ ባለሥልጣናት ና  የክልል መንግሥታትት በራሳቸው ዛሬና አሁን  “ ጃንሆይ ! “ሆነውብናል ።

ጃንሆይዎቹ ፣ ሥልጣንን ፣ ጥቅምን ፣ በአበልጅነት ፣ በሙዜነት ሣይቀር ያከፍላሉ ። አሽቃባጩን  ጨምሮ በሚገዙት ክልል ውስጥ   ፣ ዘመድ ፣ አዝማዱ  መሬት በየወረዳው እየተሰጠው በመቸብቸብ ሚሊዮነር ሆኗል ።

ዛር፣ዛሬ ፣ በዶ/ር  ጠቅላይ ሚኒሥቴር አብይ ሥልጣን ሥር ( ለምን ዶ/ር ትላለህ አትበሉ ። ዛሬ በአሣፋሪ መልኩ ዲፕሎማ ሊሰጠው የማይገባ አይደል እንዴ ማሥትሬትና ዶክተሬት ያለው ። በዕውቀት የማይታማን ሰው ማማትም ጡር ነው ። ይልቅየስ “ ሣክሥ በቃን “ ሠለቸን ። በማለታችሁ አደንቃችኋለሁ ። ) ኧረ ሥንት ጉድ ይታያል ? ሥንትና ሥንት ጉድሥ ይሰማል ? “…ታንታለሙ በጉጂ በኩል ወደኬንያ ተጋዘ ።ደሞ እኮ ፣ ሥለ ኬንያ ታንታለም ሻጪነት ይወራል   ጅሌ ! አትሞኝ ።   እከሌ እና እከሊት  የእንትና የቢዝነስ ሸሪክ ናቸው ። ያጋበሱት ሀብት ለአሥር ተውልድ የሚበቃ ሥለሆነ ፣ ሥልጣን በመልቀቃቸው ተደስተዋል ። ከህዝባዊ ቁጣና  መዓበል በፊት  በቦሌ በክብር መሸኘትን ማን ያገኘዋል ። “ ይሉሃል ።

ሌላው ይቀጥላል “እንትናም በአሜሪካ ኔቪ በኩል ፣ ከባይደን ጋር ተሻርኮ ወርቁን በበዙ ኩንታል ቋጥሮ ፣ የነገ መጦርያውን ብቻ ሳይሆን ዘር ማንዘሩን ለሺ ዓመትየሚደላቅቅበትን ጥሪት በአደራ አስቀምጧል  ።  ጤናዋም ጥሩ ሥላልሆነ ነገ ፣ ተነገወዲያ በቦሌ እብሥ ማለቱ አይቀርም ።  ያም ወሬኛ አጃቢው ሆኖ ለትምህርት ይባልና አብሮ መሄዱ ሳይታለም የተፈታ ነው ። “ ይልሃል ። “ እሽ  ሌላስ የለህም ?  ትርትሩ ! ጋ ሼ ቆርጦ ቀጥል ! “ ብትሉት በእናንተ ያለማመን እየሳቀ   ጥሏችሁ ይሄዳል ።

አንዳንዴ ፣ ″ ምነው ጆሮ ባልኖረኝ ! ″ ብላችሁ እሥከምትማረሩ ድረስ  ፤ ″ አይኔ ግንበር በሆነ ! ″ ብላችሁ ራሳችሁን እሥክትረግሙ ድረስ ፤ በአገረ ኢትዮጵያ፣ ከከንቲባ ጀምሮ ያሉ ሹመቶች በትውልድ ቦታ ፣  በሥጋ ዘመድ ፣  ፣ በሠፈር ፣ በአበልጅ ፣ በሙዜ እና በልቶ የሚያበላ ፤ በሚል የዘረፋ ደቀመዝሙርነት እየተገመገመ ፤ በክልል በለሥልጣናት  ሲሰጥ ና   አጫፋሪው ሣይቀር ፣ በሦሥትና በአራት አመት ውስጥ ወደ ቢሊዮነርነት ሊሸጋገር አንድ ሃሙሥ ቀርቶት ሥታዩ ፤ “ እንዴ ! እንዴት እንዲህ ዘረፋው ከረረ ? የወያኔ   አዳፍኔ ፤  በምን ቅፅበት    ብልፅግናንን ወረሰው ! “ ማለታችሁ አይቀርም  ።

መገረማችሁን ወደ ሰላማዊ ትግል መቀየር እና  “  ለምንድነው የእኛ ፖለቲከኞች በዓለም አገራት ዜጎች ፈፅሞ በማይስተዋል መልኩ ሰው መሆናቸውን ዘንግተው ወይም ለሆዳቸው  በማድላት  ፣ እንደእንሥሣ ለማሰብ እና በቋንቋ ተቧድነው ፣  የኔ ቋንቋ ትልቅ ነው ፣ እኔ በቋንቋዬ ልዩ በመሆኔ ብቻ ከሌላው ሰው እለያለሁ እናም የላቀ መብት አለኝ    ። ″ በሚል ሣይንሣዊም ሆነ ኃይማኖታዊ እውነት እና በሰው ለሰው መስተጋብር ውሥጥ ፣ ዓለማቀፋዊ ቅቡልነት በሌለው ፣  የአየር ላይ ፣ በመዳከር ፤ በውሥጥም ሆነ በውጪ ጎራ ለይተው ፣ከዛሬው ሥልጡን ሰው  የአሥተሣሠብ ደረጃ ዝቅ በማለት ፣  ዛሬም አገሪቱን ና ህዝቧን ሠላም እየነሷት የሚገኙት  ?  በማለት ብጠይቁና “ ሀገር በጭለማ ውሥጥ በደመነፍስ እየተወራጩ ባሉ ፣ የሚሰሩትን በማያውቁ ፣ ለሆዳቸው በተደራጁ ቡድኖች እሥከመቼ የኋሊት ሩጫ ተሮጣለች ? “ በማለት ይኽንን ወደ ገደል የሚወስድ ሩጫ ለማሥቆም በየፈርጃቸው  ጥረት ብታደርጉ መልካም ይመሥለኛል ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በሴቶች ላይ የሚደርስ የኃይል ጥቃት በአስቸኳይ ይቁም - ከአኒሳ አብዱላሂ

ሠላማዊ ትግል ዛሬ ና አሁን በእጅጉ ያሥፈልገናል ። ይኽ ትውልድ ገዢዎችን የሚሞግት እንደሆነ በተግባር ያሳያልም ብዬ ተሥፋ አድርጋለሁ ። ፈጣሪ  የፊታችንን  ቢያውቅልንም ዛሬ እየኖርነው ያለው ህይወት እጅግ አሳፋሪና  አስፈሪ ነው ።  እምነታችንን ከበሉ ፤ ልጆቻችንን ከበሉ ፤ ሀብትና ንብረታችንን ከበሉ ፤ ካወመኑ ጋር ያለ አንዳች ፍትህ የአገረ መንግሥቱ ዘዋሪዎች ፣ ባለሥልጣናቱ  ታርቀዋል ።

እርቁ የተደረገው በአውሮፖና በአሜሪካ መንግሥታት  ጫና  ነው ተብሎ ይገመታል ።  ለእነዚህ መንግሥታት ሥልጣን የሰጣቸው የአገራቸው ዜጋ ወይም ህዝብ ነው ። እናም  በየምክር ቤቶቻቸው “የፍትህ  ጥያቄ ለምን አልተመለሰም ፣ ሠለሰላም ሥናወራ ፣ ፍትህና ዴሞክራሲን ጨፍልቀን ከሆነ ታጥቦ ጭቃ ነው ። ነገሩ ና በግል ለራሳችሁ ጥቅም ካላሰባችሁ በሥተቀር ፣ ፍትህና ዴሞክራሲን በኢትዮጵያ ለማንበር እውነተኛ ና ተጠያቂነትን ያካተተ እርቅ እንዲፈጠር ታደርጉ ነበር ። “ ብሎ መጠየቁ አይቀርም ። ህዘብም በምርጫ ወቅት በካርዱ ይቀጣቸዋል ።

የኢትዮጵያ ህዝብ ግን ፣ የዛሬዎቹን ባለሥልጣናት  በምርጫ እንኳን ለመቅጣት ፣ የሚያሥችል ህገ መንግሥታዊ ነፃነት የለውም ። ለምን ቢሉ ፣ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠረው ዜጋ መራጭ እንጂ ተመራጭ የሚህንበት ፍትሃዊነትን ያነበረ የመወዳደሪያ ሜዳን ህገ መንግሥቱ ባለመፍጠሩ አንዱ በቋንቋ ሥም ገዢ ሌሎች ተገዢ ሆነዋልና ። ይኽ ብቻም አይደል  የአዳፍኔ ኔት ወርክ ከቀበሌ ጀምሮ መዘርጋቱ በየአምሥት ዓመት የሚመጣውን አገራቀፍ ምርጫ ተአማኒነቱን ይቀንሰዋል ።

ያም ሆነ ይህ በፍቅርና በህብረት መኖርን የምንወድድ  ዜጎች ፣ ምንም ሰብዓዊ መብታችን የምናስከብርበት መፈናፈኛ በህገ መንግስቱ ውስጥ አልተቀመጠልንም ። በዚህ በሸፍጥ በተሟላ ህገ መንግሥት እና በኔት ወርክ በመደራጀት ሁሉም ለዘረፋ በሚሯሯጥበት ሥርዓት ውሥጥ ፣ “ በዓለም አቀፍ ጫና ጦርነቱ ቆመ ። የሠላም ሥምምነት ተፈረመ ። “ ተብለናል ። ሠላም ለደሃው ዜጋ በመላ መምጣቱ እልል ያሰኛል ። የሚገርመው ግን “  ዜጎች እንዲጨፈጨፉ ትዕዛዝ የሰጡ ወንጀለኞች   ያለመጠየቃቸው ነው ።

ኢትዮጵያዊነታቸው  ጭምር የካዱ  ፤ የእናት አገርን ፣ ሀብቷን ብቻ በመውደድ በጎጣቸው እየማሉ ፣ ለዘረፋ ህዝብን አሰማርተው የሠላማዊ ዜጎችን ሀብትና ንብረት ካዘረፉ  ፤ ዜጎቻችንን በደቦ እንዲደፈሩ በማድረግ ፣ ካዋረዱ ፣  ( የኢትዮጵያን መከላከያ አባላትን  እና ዜጎችን  አካለ ጎዶሎ ካደረጉ  … ተዘርዝሮ የማያልቅ ግፍ በዚህ ፣ በዘመነ ፣ 21 ኛው ክፍለ ዘመን ፣ በየዋሁ እና በኃይማኖተኛው ህዝብ ላይ ከፈፀሙ …)  ሰው መሠል አራዊቶች ጋር ፣ ያለ አንዳች ፍትህ  ″ ለሠላም ሲባል ሁሉንም ነገር ይቅር ብለናል ። ″ ማለት ፤ ምን ማለት ነው ? የመንግሥት ባለሥልጣናት እግዜር ናቸው እንዴ ?

” ጁንታ እና የናት ጡት ነካሽ ” ተብሎ ከተፈረጀው በንፁሃን ደም እጁ ከተጨማለቀ  ጋር ያለ ” ኢትዮጵያ ህዝብ ይሁንታ ! ” ታርቀናል  ። ብሎ መሞዳሞድን ከማየት ፣ በእውነቱ ” በዚህ ፍትህ በተቀበረችበት ዘመን ምነው ባልተፈጠርኩ  ?! ” የሚያሰኝ ነው ።

በነገሬ ላይ ልባዊ ዕርቅን የሚጠላ የለም ። ይቅር መባባል የሠላም መሠረት ነው ። ሆኖም ሳያውቁ በወያኔ መሪዎች አሥገዳጅነት ወይም እንጀራ በልተው ለመሠንበት ባላቸው ሰብዓዊ ጉጉት  ፣ የህውሀትን የጦርነት ትዕዛዝ የፈፀሙ ፣ ልዩ ኃይሎች ፣ ሚሊሻዎች ፣ የትግራይ ወጣቶችና ሽማግሌዎች ፣ በደሉ በግበር ቀደም ፣ ከደረሰበት የአፋር ና የትግራይ ህዝብ ጋር ፣ ” መሪዎቻችን ለሥልጣናቸው ሲሉ  በሐሰት ትርክት ወደ ጦርነት አሥገብተውን ፣ ምንም ያልበደላችሁንን ወንድምና እህቶቻችንን ለሥቃይና ለሥደት በመዳረጋችን  ይቅር ለእግዛብሔር በሉን ። ” ሊሉና ለሠላም ሲባል ይቅር ሊባባሉ ይችላሉ ።   ማንም ህሊና ያለው ፍጡር ይህ እውነት  አያቀረሸውም ። …

ተጨማሪ ያንብቡ:  ምልጃ ! አማልዱኝ!! አማልዱኝ ‘ባካችሁ!!! - ኮማንደር አሰፋ ሰይፉ

ገዢው ፖርቲ  ብልፅግና ፣ ” የእናት ጡት ነካሽ ” እያለ ሲጠረው የነበረን አገር አፍራሽ ተላላኪ ቡድን ፤ ወንድምና ወንድምን አጋዳይ ሤጣን ቡድን  ፤ ” እሥከ ሥሙ ይጥፋ ! እንደ አያ ጅቦ    ወያኔ  የተሰኘ ሥም ለመጪው ትውልድ ማሥፈራሪያ ይሁን ! ! ”  ተብሎ በአደባባይ የተወገዘን ቡድን ግን ይቅር ማለት ህዝቡን ከማቀርሸትም አልፎ የጨጎራ ህመምተኛ አድርጓታል ። እርር ድብን ነው ፣ ያለው ። አብሶ ከመለስ ዜናው ጊዜ ጀምሮ በማሥመሠል በተካኑ ሰዎች ለሠላም ሲባል ያለ አንዳች ፣ ፍትህና ካሣ ፣ ከሁለቱም ወገን በጠፉ ዜጎች መቃብር ላይ ቆመን ሠላምን ፈጥረናል መባል እጅግ ያማል ።

ከመለስ ዜናዊ አምባገነናዊ አገዛዝ ጀምሮ ጭራቸውን በመቁላትና እንደመለሥ ካልተናገርን ሞትን እንገኛለን ከሚሉ ( ዛሬም ያ ማሥመሠላቸው በግልፅ ይታያል ። ) አስመሣዩ ጭራቸው ፣ ዛሬም ድረስ ረዝሞ የሚታይ ጉድች ፤  በቃላት ጭምር  ከአዋረዳቸው ጌታቸው ረዳ እና ከናቃቸው ደብረፅዮን ጋር ሲተቃቀፉ ማየት ፣ ለዚች ሰንደቅ ፣ ለዚች አገር ፣ ለዚች ምሥኪን እናት አገር ብለው የተሰው ጓዶቻቸውን ፣ ልጆቻቸውን ፣ ወገኖቻቸውን  ለማይረሱ ሁሉ የሞት ሞት ነው ።

ከዚህ ውርደት ከማይገልፀው ደባሪ  ኩነት አንፃር  አሁን ያለንበት ሁኔታ በታሪክ እጅግ የጠቆረ ” አሥጠሊ እና አሣፋሪ “ተብሎ  ይመዘገባል ። …

አንድ የታሪክ አደራ ያለበት ይትልቅ አገር መንግሥት  በግፈኞች  ለተሰቃዩት ፣ ለተዋረዱት ፣ ለቁሰሉት ፤ በሁለቱም ወገን በጦርነቱ ሰበብ  ለሞቱት ከ600 ሺ  በላይ ዜጎች ፤ ለቆሰሉትና  አካለ ሥንኩል ለሆኑት ከ 50  ሺ በላይ ዜጎች ፣ ( በግምት )  እንዴት ፍትህን ይነፍጋቸዋል ? ህዝብ ለአገር ሉአላዊነት ፣ ለነፃነቷና ለክብሯ እንጂ  ለግለሰቦች ብሎ እኮ ከንቱ መሰዋትነት አልከፈለም ። መንግሥት ይኽንን እውነት  እያወቀ ሌላ አጀንዳ በመፍጠርና በማደናገር  ከዘለቀም “ እንደ ሁለቱ አሥቂኝ ለማኞች ወግ “ ድርጊቱን በትዝብትና ያለአዋቂነት ነው ። በማለት  በመሳቅ  አናልፈውም ።

″ የሁለት ለማኞች ወግ ″ የጽሁፉ ማሰረጌ

በጊዮርጊስ  ቤተክርስቲያን በራፍ ላይ ሁለት የእኔ ብጤዎች ጎን ለጎን ሆነው ይለምናሉ ።   አንዱ ለማኝ  ጀማሪ ና የዋህ ለማኝ ነው ። ፊደል ያለቆጠረ ከመሆኑም በላይ ሥለ ኃይማኖት የጠለቀ ዕውቀት የለውም ። አጠገቡ ያለው ደግሞ የ30ውንም ቀን  ድርብና ነጠላ የመላእክት ና የሰማዕታትን ቀን ጠንቅቆ የሚያውቅ ነው ።

ዕለቱ ጊዮርጊስ እንደመሆኑ ይኼ የነቃው የእኔ ብጤ ” ጋሼ ! አባባ ! ልጄ! ሥለ ፈረሰኛው ጊዮርጊስ ! ሥለ ፈረሰኛው ጊዮርጊስ ! …” እያለ ሲለምን ይሰማል ጎኑ ያለው የዋህ ለማኝ ። ከእርሱ ለየት አድርጌ መለመን አለብኝ በማለት ፣ ” ሰለ ፈረሰኛው ገብርኤል ! ሥለ ፈረሰኛው ገብርኤል ! …” እያለ መለመን ሲጀምር ፣ አጠገቡ ያለው የነቃው ለማኝ ” ገብርኤል ፈረስ የለውም ። ” ይለዋል ። ይኽንን እንደ ሰማ አጠገቡ ያለው ለማኝ ደንግጦ ” ወይ ! በምትኩት ! ነበረው እኮ ! ቸግሮት   ሸጠው እንዴ ?! ” አለ ይባላል ።

መቼም መላዕክት  ሰው እንዳይደሉ ይታወቃል ። ተጠሪነታቸውም  ለኃያሉ እግዚአብሔር ነው ። መንግሥትሥ  ተጠሪነቱ  ለህዝብም  አይደል ?

1 Comment

  1. እንደ እኔ ዋና ተጠያቂ ህወአት የሚሉት አራጅ ቡድን ሲሆን ሁለተኛ ተጠያቂ የሳይበር አዝማቾች የትግሬ አክቲቪስቶች ናቸው በተለይም ቴዎድሮስ ጸጋዬ፤አሉላ ሰለሞን፤ስታሌን የተባሉት ነብሰ ገዳዮች በሰው ስቃይ የሚደሰቱ ናቸው ከዛ በመቀጠል የትግሬ ነብሰ ገዳዮች እንዳይጠፉ ሊጠፉ ሲል የሚያድናቸው አብይ መሃመድ ነው፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.